ዜና፡ በኮንሶ ዞን የተከሰተውን ረሃብ ለማስታገስ ድጋፍ ተጠየቀ ፣ ሕፃናት ሞተዋል ፣ ከ190 ሺህ በላይ ሰዎች ለረሃብ ተጋልጠዋል

ምስል፡ በኮንሶ ዞን የተከሰተውን ረሃብን ከሚያሳይ ቪዲዮ የተወሰደ

በብሩክ አለሙ

አዲስ አበባ፣ሃምሌ 8፣ 2014 ዓ.ም ፦የኮንሶ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበዬሁ በዞኑ ውስጥ በተፈጠረው ግጭት እንዲሁም በድርቅ ምክንያት የበርካታ ሰዎች ሞት ፣ መፈናቀል፣ እና ከፍተኛ ንብረት ውድመትን ተከትሎ ህብረተሰቡ ለከፋ የረሃብ አደጋ በመጋለጡ የተለያዩ ግብረሰናይ ድርጀቶች ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

በቅርቡ በዞኑ 13 ህጻናት በረሃብ መሞታቸው ተዘግቧል። በተጨማሪም በዞኑ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ያለባቸው ህጻናት ቁጥር እየጨመረ ሲሆን ከ240 በላይ የሚሆኑት ወደ ሆስፒታሎች ገብተዋል።

የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ በዞኑ ከሚንቀሳቀሱ ግብረሰናይ ድርጅቶች ጋር በጉዳዩ የመከሩ ሲሆን በምክክሩም በዞኑ የሚንቀሳቀሱ ግብረሰናይ ድርጅቶች ለህብረተሰቡ በርካታ ድጋፍ ቢያደርጉም ከጉዳቱ ስፋትና ብዛት አንጻር አሁንም ብዙ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል።

በግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋትና ቅድሜ ማስጠንቀቂያ በሰራው ዳሰሳ ጥናት ከ190 ሺህ ህዝብ በላይ ለረሃብ እንደተጋለጡ መሆኑን የገለፀ ሲሆን በኮንሶ የሚንቀሳቀሱና እየደገፉ ያሉ መንግታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አሁን የተከሰተውን የረሃብ አደጋ ለመከላከል እንዲያግዙ የጽ/ቤቱ ኃላፊ አቶ ገደኖ ከዋይታ ጠይቀዋል።

አቶ ገደኖ ከዋይታ አክለመውም በዞኑ 3 ጤና ኬላ፣ 12 የቤተ ክርስቲያን፣ 14 ትምህርት ቤቶች ሙሉ በሙሉና በከፊል በግጭቱ መውደማቸውን ተናግረው ከመቶ ሺህ በላይ እንስሳት የመኖ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው አብራርተዋል።

የኮንሶ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ከፈነ ትጫሮ በበኩላቸው በዝናብ እጥረት ምክንያት የተከሰተው ረሃብን ጨምሮ በግጭት ምክንያት የተፈናቀሉ ዜጎችን ለማገዝ በዞኑ የሚቀሳቀሱ ግብረሰናይ ድርጀቶች አሁናዊ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።

በኮንሶ ዞን የምርት ዘመን በአራቱ ዋና ዋና የሰብል ዓይነቶች ከተዘራዉ 96,157.3 ሄክታር መሬት 24,202 ሄክታር ምርት በድርቅ በመጥፋቱና የመኸር እርሻ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲቀንስ ምክንያት በመሆኑ ህብረተሰቡን ለረሃብ መዳረጉን የኮንሶ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋትና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ጽ/ቤት ባለሙያ አቶ ዘርፉ ላቀው ባለፈው ሳምንት ገልፀዋል፡፡

የደቡብ ክልል የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ጋንታ ጋምኣ በኮንሶ ዞን በተለያየ ወቅት በተፈጠሩ ግጭቶች ምክንያት ለተፈናቀሉ እንዲሁም ሰብላቸው በዝናብ እጥረት ምክንያት ለተጎዳባቸው ሰዎች የምግብ እርዳታ እየቀረበ መሆኑን የገለፁ ቢሆንም ነዋሪዎቹ ግን የመንግስት እርዳታ በመጠባበቅ ላይ ነን ብለዋል፡፡ የዞኑ ዋና የመንግሥት ተጠሪ አቶ ተስፋዬ በበኩላቸው የሴፍቲኔት እርዳታው እየቀረበ ቢሆንም በቂ አለመሆኑን ያስረዳሉ።

እስካሁን በዞኑ የሚንቀሳቀሱ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ከዞኑ መንግስት ጋር በመተባበር ያደረጉትን እና እያደረጉ ያለውን ድጋፍ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ አድንቀዋል።

በያዝነው አመት ሚያዚያ ወር ከዚሁ ኮንሶ ዞን በተከሰተ የርስ በርስ ግጭት ከአስር ቀበሌዎች ህፃናትን እና ሴቶችን ጨምሮ ወደ 37,000 ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን አዲስ ስታንዳርድ መዘገቧ ይታወሳል። ከነዚህም ውስጥ ከ32,000  ሰዎች በላይ ከሰገን ዙሪያ ወረዳ፣ ከ3,000 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ከደራዜ ወረዳ ከካራት ዙሪያ እንዲሁም ቀሪዎች 1,000 ደግሞ ከቦርቃራ እና ማታራጊዛባ ቀበሌዎች ለሳምንታት በዘለቀው ግጭት መፈናቀላቸውን በዘገባው ተጠቅሶም ነበር።  አስ 

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.