ዜና ትንታኔ፡ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ከነገ ጀምሮ ተግባራዊ የሚደረግ የታሪፍ ጭማሪ አደረገ፣ የምጣኔ ሀብት ባለሙያው የነዳጅ ድጎማ መነሳቱ አደገኛ ውሳኔ ነው አሉ

በአዲስ አበባ ከተማ ለታክሲዎች ወረፋ የዕለት ተዕለት ክስተት ሆኖ እየታየ ነው።

በብሩክ አለሙ

አዲስ አበባ ሃምሌ 6፣2014 ዓ.ም ፦ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ወቅታዊ የነዳጅ መሸጫ ዋጋ ለውጥን ብቻ መሰረት በማድረግ በሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ ለተሰማሩ የሚዲ-ባሶች እና የሚኒ-ባስ ታክሲዎች የአገልግሎት ታሪፍ ማስተካከያ ከነገ ሐምሌ 7/2014 ዓ.ም ጀምሮ ከ0.50 ሳንቲም እስከ 6 ብር የሚደርስ ጭማሪ አድርጊያለው ሲል ቢሮው አስታውቋል፡፡ በዚህም መሰረት በሚዲ-ባስ ከ0.50 ሳንቲም እስከ 2.00 ብር የተጨመረ ሲሆን በሚኒ-ባስ 0.50 እስከ 6 ብር ጭማሬ መደረጉን ገልጿል።

ቢሮው በተደረገው የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ የተነሳ ባሳለፍነው ወር በታክሲዎች ላይ ከ50 ሳንቲም እስከ 3 ብር ከ50 ሳንቲም ጭማሪ ማድረጉ ይታወሳል፡፡

መንግሥት የነዳጅ ምርቶችን ለመደጎም በየወሩ በአማካይ 10 ቢሊዮን ብር ወጪ እያደረገ ለረጅም ዓመታት መቆየቱንና በአሁኑ ወቅት 147 ቢሊዮን ብር ገደማ ለነዳጅ ድጎማ ያዋለው ገንዘብ ዕዳ እንዳለበት ገልፀል። ይህንንም ማስቀጠል አዳጋች ስለሆነበት ድጎማውን ቀስ በቀስ ለማንሳት ውሳኔ አሳልፎ ባለፈው ሳምንት ከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ተደርጓል።

ይህ በዚህ እንዳለ የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶክተር ጉቱ ዋሱ ይህን የነዳጅ ድጎማ የመነሳት ውሳኔ አደገኛና የተሳሳተ እርምጃ ሲሉ ለዶቸ ቬሌ አማርኛ ተናግረዋል። ክረምት በመጣ ቁጥር ለብርዱ ተፈላጊዋ የበቆሎ እሸት እንደወትሮው በአነስተኛ ገንዘብ የሚቀመስ አልሆን እያለ የመጣ ይመስላል። አንድ ዛላ በቆሎ ተጠብሶ በ20 ፣ ተቀቅሎ ደግሞ በ25 ብር እየተሸጠ ይገኛል። ከሦስት እና አራት ወራት በፊት ባንኮች ለደንበኞቻቸው ብድር ፈቅደውላቸው ይደረግ በነበረ ግብይት ከአዲስ አበባ ጫፍና ጫፍ በታነፁ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የባለ ሁለት መኝታ 70 ካሬ የጋራ መኖሪያ ቤት እስከ 2.7 ሚሊዮን ብር ሲሸጡ ነበር። አሁን ይህን መሰሉ ቤት እስከ 3.5 ሚሊዮን ብር ይሸጣል የሚለው የቤት ግብይት አሳላጭ ደላላ የኑሮው ውድነት የፈጠረውን የገንዘብ የመግዛት አቅም ማነስ በቁጥር አስደግፎ ለ ዶቸ ቨለ ተናግሯል።

“በአገሪቱ ውስጥ እየተንሰራፋ የመጣውን ሥርዓት አልበኝነት እና የሰላምና መረጋጋት መጥፋቱን መንግሥት ማስትካከል ይችል ነበር”

ዶክተር ጉቱ ዋሱ

የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶክተር ጉቱ ዋሱ እንዳሉት የዚህ ወር የዋጋ ንረት ካለፈው ዓመት ለንጽፃሬ ሲቀርብ ሸቆጦች ዋጋቸው እጥፍና ከእጥፍ በላይ ጨምሯል። አንዱ የዚህ የዋጋ ጭማሪ ምክንያት ደግሜ የነዳጅ ዋጋ መጨመር ነው፡፡ እናም አሁን በዚህ የኑሮ ውድነት ምክንያት ከ30 ሚሊዮን ሕዝብ በላይ ከነበረበት የድህነት ወለል በላይ ወደ ከድህነት ወለል በታች ወርዷል ብለዋል። ስለዚህም የመንግሥት ውሳኔ ተገቢነትና ምክንያታዊነት ይጎድለዋል ሲሉ ይከራከራሉ።

“በኢትዮጵያ ውስጥ ለተከሰተው ማንኛውም የምጣኔ ሀብት ቀውስ የመጀመሪያው ተጠያቂ መንግስት ነው” የሚሉት የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶክተር ጉቱ “በአገሪቱ ውስጥ እየተንሰራፋ የመጣውን ሥርዓት አልበኝነት እና የሰላምና መረጋጋት መጥፋቱን መንግሥት ማስትካከል ይችል ነበር” በማለት ይህ አለመደረጉ መሰረታዊ አባባሽ ችግሮች መሆናቸውንና ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ላይ አለማተኮርንም ሊስተካክል የሚገባ እንደነበር ይዘረዝራሉ።

የነዳጅ ድጎማው መነሳት በአብዛኛው ከትራንስፖርት አገልግሎት ጋር ብቻ ሲያያዝ ይስተዋላል። ይሁንና የኤሌክትሪክ አቅርቦት በስፋት በሌለባቸው ቦታዎችና በኃይል መቆራረጥ ምክንያት በጀነሬተሮች ለመስራት አማራጭ የሚጠቀሙ ሰፊ የሥራ መስኮችንም ጭማሩው ማስጨነቁ አይቀርም። ከሕዝብ ትራንስፖርት ባልተናነሰ ከፍተኛ ግልጋሎት ሰጪዎቹ የጭነት ተሽከርካሪዎች የድጎማው ዘላቂ ተጠቃሚ አለመሆናቸውም ኑሮን የባሰ አባባሽ መሆኑ እንደማይቀር ይታመናል።

አዲስ ስታንዳርድ የነዳጅ ጭማሬው ህብረተሰቡ ላይ ያስከተለውን የኑሮ ውድነትና የትራንስፖርት ተፅዕኖ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎችን እና የታክሲ አሽከርከሪዎችን በማነጋገር ዘገባ ማቅረቡ የሚታወስ ነው፡፡ ከዘገባውም መረዳት እንደታቻለው መንግስት በነዳጅ ላይ የዋጋ ጭማሪ ባደረገበት ማግስት ነጋዴውና የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጭዎች በህበተሰቡ ላይ የራሳቸውን ጭማሬ ሲያደረጉ በመቆየታቸው ቀድሞውኑ ለህዝቡ ከባድ የነበረውን የኑሮ ውድነት ይባስ እንዲያሻቅብ ማድረጉንም ነው፡፡

ሃሳቡን ለአዲስ ስታንዳርድ ያካፈለው አንድ የመዲናዋ ነዋሪ የነዳጅ ጭማሬው በነዋሪው ላይ ትልቅ ተፅእኖ መፍጠሩን ካለው የሸቀጦች ሽመታ ጋር በማያያዝ “እቃ ለመግዛት ስትሄድ ሻጮቹ ነዳጅ ስለጨመረ እቃ የሚያመጡልን ተሸከርካሪዎች ጭማሬ በማድረጋቸው እኛም ጨምረናል ይሉሃል፡፡ ነዋሪው በሚጠቀመው ትራንሰፖርትና በሸቀጦች ላይ ተገቢ ያልሆነ ክፍያን ለመክፈል እየተገደደ ነው “ ሲል አስረድቷል፡፡

የታክሲ ሹፌሮችም በበኩላቸው መንግስት በነዳጅ ላይ የዋጋ ጭማሬ ማድረጉን እንጂ ባለ ታክሲዎች ላይ የሚመጣውን ተፅዕኖ ከግንዛቤ ውስጥ አላስገባም ሲሉ ይናገራሉ፡፡ “የነዳጅ ጭማሬውንና ድጎማውን ምክንያት በማድረግ የመኪና መለዋወጫ እቃዎች ላይ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሬ ተደርጎብናል፡፡ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል መፍትሄ ሊሰጠን ይገባል” ሲሉ በምሬት ገጸውልናል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.