ዜና፡ 20ሺ የሚጠጉ ከሱዳን ተሰደው በመተማ በኩል የገቡ ኢትዮጵያውያን ትራንስፖርት ተዘጋጅቶላቸው ወደ መዳረሻቸው መሸኘታቸውን ተመድ አስታወቀ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 2/2015 ዓ.ም፡- ሁለተኛ ወሩን ለመድፈን የተቃረበው የሱዳን ተፋላሚ ሀይሎች ውጊያ አሁንም አልቆመም። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሰኔ 2 ቀን 2015 ዓ.ም ያወጣው ወቅታዊ ሪፖርት እንደሚያሳየው ከሆነ ወደ ኢትዮጵያ የገቡ የሱዳን ስደተኞች ቁጥር ከ41ሺ በላይ ሁኗል። አብዘሃኛዎቹ ስደተኞች ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ያስታወቀው የመንግስታቱ ድርጅት ሪፖርት በየቀኑ ከ700 እስከ አንድ ሺ የሚደርሱ ስደተኞች በመተማ በኩል የኢትዮጵያን ድንበር አቋርጠው እንደሚገቡ ጠቁሟል።

በቁጥር 19 ሺ 500 የሚደርሱ በሱዳኑ ግጭት ቤታቸውን ጥለው ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ኢትዮጵያውያን ወደ ትውልድ መንደራቸው የትራንስፖርት አገልግሎት ተዘጋጅቶላቸው መሸኘታቸውን የተመድ ሪፖርት አመላክቷል።

በመተማ በኩል ከገቡ ስደተኞች መካከል ከአራት ሺ በላይ የሚሆኑ ስደተኞች በመጠለያ እንደሚገኙ የጠቆመው የመንግስታቱ ድርጅት ሪፖርት መጠለያው በመጨናነቁ ምክንያት በየግዜው ወደ መግቢያ ጣቢያው በሚመጡ አዲስ ስደተኞች ላይ የጤና እና ደህንነት እክል እንዳያጋጠማቸው ስጋት እንደገባው አስታውቋል።

በመተማ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለሚገቡ ስደተኞች ትኩስ ምግቦች፣ የመጠጥ ውሃ እና የጤና አገልግሎት እየቀረበላቸው እንደሚገኝም ገልጿል።

በተያያዘ ዜና በሱዳን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ልዩ ልዑክ ቮልከር ፐርዘስ የለመከሰስ መብታቸውን እንደገፈፈው አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን አስታውቀዋል።  የሱዳን ላዕላዊ ምክር ቤት ፕሬዝዳን አልቡርሃን ከሁለት ሳምንታት በፊት ልዩ ልዑኩ በሱዳን ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ግጭቱ እንዲባባስ እያደረጉ ነው የሚል ትችት ማሰማታቸውን እና በዚያውም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት እንዲያነሳቸው ጠይቀው እንደነበር ዘገባዎቹ አውስተዋል።

የሱዳን መንግስት በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኩል እንዳስታወቀው ከሆነ የመንግስታቱ ድርጅት የሱዳን ተወካይ ቮልከር ፐርዘስ በሱዳን መነግስት እንደማይፈለጉ እና ያለመከሰስ መብታቸው መነሳቱን አመላክቷል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.