ዜና፡ ቤተክርስቲያኗ የዘጠኝ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት ሰጠች፤ በትግራይ አባ ሰረቀብርሃንን ጨምሮ አስር አባቶች ለኤጲስ ቆጶስነት መመረጣቸው ተገለጸ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 10/2015 ዓ.ም፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በኦሮምያ እና በደቡብ ክልል ለሚገኙ ሀገረ ስብከቶች የሚመደቡ የዘጠኝ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት መስጠቷ ተገለጸ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ለዘጠኙ ኤፒስ ቆጶሳት ሹመቱን የሰጡት በመንበረ ፓትሪያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም መሆኑን ታውቋል። ብጹዕነታቸው የኤጲስ ቆጶሳቱ ሹመት በሰጡበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት “ቤተክርስቲያኒቷ ውስጥ ባልተጠበቀ እና ባልተለመደ ሁኔታ ብቅ ብቅ ሲሉ የሚታዩት ራስን በራስ የመሾም አባዜ መገታት አለባቸው፤ ማንኛውም ችግር በውይይት፣ በምክክር እና የተበደለውንም በመካስ መፈታት ይገባዋል ብለዋል።”

ሹመቱ የተሰጠባቸው ሀገረ ስብከት እና አባቶችም በዝርዝር ተገልጿል። በዚህም መሰረት አባ ክንፈ ገብርኤል ተ/ማርያም አባ ገሪማ ተብለው የጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጅ ሀገረ ስብከት፣ አባ ሳህለ ማርያም ቶላ አባ ገብርኤል ተብለው የምዕራብ ሸዋ ሀገረስብከት፣ አባ ስብአት ለአብ ሀይለማርያም አባ ጢሞቲዎስ ተብለው የዳወሮ ኮንታ ለገረ ስብከት፣ አባ አምደሚካኤል ሀይሌ አባ ኤልሳዕ ተብለው የምስራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት፣ አባ ሀይለማርያም ጌታቸው አባ በርቶሎሜዎስ ተብለው የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት፣ አባ ጥላሁን ወርቁ አባ ኤፍሬም ተብለው የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት፣ አባ ዘተ/ሀይማኖት ገብሬ አባ ኤጲፋንዮስ ተብለው የሆሮ ጉድሩ ሀገረ ስብከት፣ አባ እስጢፋኖስ ገብሬ አባ ዳንኤል ተብለው የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት እና አባ ወ/ገብርኤል አበበ አባ ኒቆዲሞስ የምስራቅ ሀረርጌ ሀገረ ስብከት ሆነው ተሹመዋል።

በሌላ ዜና የትግራይ የቤተክርስቲያኗ አባቶች በቀጣይ በትግራይ ክልል እና በሌሎች ሀገራት በሚገኙ ቤተክርስትያናት እንዲያገለግሉ በሚል አስር አባቶችን የኤጲስ ቆጶሳቱ ሹመት ለመስጠት በትላንትናው እለት ምርጫ አካሂደዋል። መንበረ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን በሚል ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አደረጃጀት እራሳቸውን በማግለል ያቋቋሙት የትግራይ የቤተክርስቲያኗ አባቶች ምርጫውን ያካሄዱት በአክሱም ከተማ መሆኑን የክልሉ መገናኛ ብዙሃን አስታውቀዋል።

በትግራይ በሚገኙ ሀገረ ስብከቶች እንዲያገለግሉ አምስት አባቶች የተመረጡ ሲሆን እነሱም መጋቤ ሃዲስ ቆሞስ ኣባ ዘሥላሴ ማርቆስ፣ መልኣከ ገነት ቆሞስ ኣባ ሃ/ሚካኤል ኣረጋይ፣ ሊቀ ኣእላፍ ኣባ እስጢፋኖስ ገ/ጊዮርጊስ፣ ንቡረእድ ቆሞስ ኣባ መሓሪ ሃብቴ እና ቆሞስ ኣባ ኤልያስ ታደሰ ገብረኺዳን መሆናቸው ተገልጿል።

በውጭ ሀገራት ቤተክርስቲያኗን እንዲያገለግሉ አምስት አባቶች የተመረጡ ሲሆን ከነዚህም መካከል ከአውስትራሊያ ወደ መቀሌ ሲያቀኑ በቦሌ ኤርፖርት እንዳይንቀሳቀሱ ተደርገው የነበሩት ቆሞስ አባ ሰረቀብርሃን ወልደ ሳሙኤል ይገኙበታል። ቆሞስ ኣባ ሰረቀብርሃን ወልደሳሙኤል በኢትዮጵያ የጸጥታ ሀይሎች አስገዳጅነተ ወደ ሀንድ እንዲጓዙ ከተደረጉ በኋላ ወደ መጡበት ወደ አውስትራሊያ ተጉዘዋል። አውስትራሊያ ሲደርሱም በአከባቢው በሚገኙ ምዕመናን ከፍተኛ አቀባበል ተደርጎላቸዋል። ከቆሞስ ኣባ ሰረቀ ብርሃን ወልደሳሙኤል በተጨማሪ በአክሱም ለኤጲስ ቆጶስነት ከተመረጡት መካከል መልኣከ ገነት ኣባ ፅጌገነት ኪዳነ ወልድ፣ ኣባ ዘርኣዳዊት ብርሃነ፣ መልኣከ ፅሓይ ቆሞስ ኣባ ዮሃንስ ከበደ እና መልኣከ ፅሃይ ኣባ የማነ ብርሃን ወልደሳሙኤል ይገኙበታል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.