ዜና፡ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኘው ቀይ ቀበሮ የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠበት ተገለጸ፤ የማዳን ስራ እየተሰራ መሆኑ ተጠቁሟል

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 8/2015 ዓ.ም፡- በኢትዮጵያ የሚገኙ የተኩላ እንስሳ ዝርያዎች ገዳይ በሆነ ቫይረስ ሳቢያ እና መኖሪያቸው እየጠበበ በመምጣቱ የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠባቸው ተገለጸ። ሁኔታውን ለመቀልበስ የማዳን ስራ እየተሰራ መሆኑን ዲስከቨሪ ዋይልድ ላይፍ ድረገጽ ባወጣው ዘገባ አስታውቋል።

በባሌ ተራሮች ላይ የሚገኙት የቀይ ቀበሮ የተኩላ ዝርያዎች ካኒን ዲስቴምፐር (Canine Distemper Virus) የተሰኘ ገዳይ ቫይረስ በመጠቃታቸው ህልውናቸው አደጋ ላይ መሆኑን ድረገጹ ጠቁሟል።

ቫይረሱን ለመከላከል እየተሰጣቸው ያለው ክትባት በህይወት ለመቆየት እና ከምድረገጽ እንዳይጠፉ ለማስቻል ሁለተኛ እድል እየሰጣቸው እንደሚገኝ ዘገባው አመላክቷል። የኢትዮጵያ ቀበሮ ወይንም አቢሲኒያ ቀበሮ በመባል የሚታወቀው ቀይ ቀበሮ በአፍሪካ ከሚገኙ የተኩላ ዝርያዎች እጅጉን አደጋ ላይ የሚገኝ መሆኑን ዘገባው አስታውቋል። በአሁኑ ወቅት ከ500 በታች የሚሆኑ ቀይ ቀበሮዎች ብቻ በህይወት እንደሚገኙ በዘገባው ተጠቁሟል። ቀይ ቀበሮዎቹ የሚኖሩበት አከባቢ የሚገኙ ሰዎች እየተስፋፉ እና በዚያው አከባቢ መኖር በመጀመራቸው ቀያቸው አደጋ ላይ እንደሚገኝን የድረገጹ ዘገባ ጠቁሟል።

ቫይረሱ በቀይ ቀበሮዎች ላይ የሚያደርሰውን አደጋ ለመከላከል ሲባል በአከባቢው የሚገኙ ውሻዎችም እንዲከተቡ እየተደረገ እንደሚገኝ ተገልጿል። የኢትዮጵያ የቀበሮ ጥበቃ ፕሮጀክት ከ1988 ዓ.ም ጀምሮ የቀበሮዎችን ህልውና ለመታደግ በሚል ክትባት እንደሚሰጥ የገለጸው ድረገጹ ቀበሮዎችን ለመታደር በአከባቢው የሚገኙ ውሾችንም የመከተብ ተግባር እንደሚያከናውን አስታውቋል።

የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል በፕሮጀክቱ አማካኝነት በአመት አምስት ሺ የአከባቢውን ውሾች ለመከተብ መታቀዱን ዘገባው ጠቁሟል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.