ዜና፡በአድዋ በዓል አከባበር ላይ ተፈጥሮ በነበረው ሁከት 878 ተጠርጣሪዎች ተይዘዋል፤ ህይወቱ ያለፈዉ የአንድ ግለሰብ ጉዳይ እየተጣራ ነው – የጋራ ግብረሃይል

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነርና የፀጥታና ደኅንነት ግብረ-ኃይል አባል ጌቱ አርጋው

አዲስ አበባ፣ የካቲት 30/ 2015 ዓ.ም፡– የፀጥታ እና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል የኦፕሬሽናል ኮሚቴ ለሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው በአድዋ በዓል አከባበር ላይ ተፈጥሮ በነበረው ሁከት 878 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን በአሉን ተገን አድርገው በከተማዋ ብጥብጥ ለመፍጠር ሲዘጋጁ የነበሩ ከበዓሉ በፊትም በርካታ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ጠቁሟል።

በበአሉ ዕለት ብቻ በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል 575 የሚሆኑት ከአዲስ አበባ ውጭ ከሌሎች ክልሎች የመጡ መሆናቸውን የፀጥታ እና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል የኦፕሬሽናል ኮሚቴን በመወከል መግለጫውን የሰጡት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነርና የፀጥታና ደኅንነት ግብረ-ኃይል አባል ጌቱ አርጋው ገልጸዋል።

የዘንድሮው የአድዋ በዓል በከተማዋ በሶስት ቦታዎች መከበሩን የጠቆሙት ኮሚሽነር ጌቱ አረጋው በሚኒሊክ አደባባይ የነበረው አከባበር ከተጠናቀቀ እና መንገዶች ለተሽከርካሪዎች ክፍት ከተደረጉ በኋላ ረብሻ መፈጠሩን አምነዋል። ረብሻ የተፈጠረው በአደባባዩ አቅራቢያ በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ በቤተክርስቲያኑ የነበረውን የበዓል ዝግጅት ተገን በማድረግ ወደ ቤተክርስቲያኑ የገቡ ረብሻ ፈጣሪዎች ያልተለመዱ አይነት መልዕክቶች የያዙ መፎክሮችን ለማሰማት ሙከራ አድርገው እንደነበር ተናግረዋል።

ወደ ቤተክርስቲያኗ ቅጥር ግቢ በመግባት በጸጥታ ሀይሉ ላይ ድንጋይ በመወርወር ጥቃት መፈጸማቸውንም አመላክተዋል። ከተማዋን ለመበጥበጥ፣ በንብረት እና በሰው ላይ ጉዳት ለማድረስ የሚያስችል አጠቃላይ እንቅስቃሴ ሲደረግ ነበር ሲሉም ተናግረዋል።

ከበዓሉ ቀደም ብሎም በጥናት ተደግፈን በርካታ ሰዎችን በቁጥጥር ስር አውለናል ሲሉ የገለጹት ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው በተደረገ ፍተሻ እና ክትትል ከሸኔ ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ ተጠርጣሪዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል ብለዋል።

ከበአሉ ጋር በተያያዘ ተፈጥሮ በነበረው ሁከት የደረሰውን ጉዳት አስመልክተው እንደገለጹት አንድ የከተማው ነዋሪ በተተኮሰ ጥይት ህይወቱ ማለፉን እና ጉዳዩ እየተጣራ መሆኑን አስታውቀው በተጨማሪም በ16 የፖሊስ አባላት ላይ ቀላል እና ከባድ ጉዳት ደርሷል ብለዋል።

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌቱ አረጋው ለሀገሪቱ መገናኛ ብዙሃን እንዳስታወቁት በመዲናዋ ሰላም ወዳድ እንዳለ ሁሉ አቅደው የሚሰሩ ጸረ ሰላም ሀይሎች አሉ ሲሉ ገልጸው ለእኩይ አላማቸው ማስፈጸሚያ የብሔር የሀይማኖት በአላትን ይጠቀማሉ ብለዋል። በመሆኑን የእምነት ተቋማቱም ሆኑ ሰላም ወዳዱ ማህበረሰብ የከተማዋን ሰላም ለማስከበር ከጸጥታ ተቋማት ጋር እንዲሰራ ጥሪ አቅርበዋል።

በ127ኛው የዓድዋ ድልን ለማክበር በምኒልክ አደባባይ በተሰበሰቡ ነዋሪዎች ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች አላስፈላጊ እና ከመጠን ያለፈ እርምጃ መውሰዳቸውን እና በዚህም የአንድ ሰው ህይወት ማለፉን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የካቲት 24/2015 ዓ.ም ባወጣውመግለጫ አስታወቆ ነበር። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.