ዜና፡ በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ መሰረት 23 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ተገለፀ

አዲስ አበባ፣ ነሃሴ  5/ 2015 ዓ.ም፡- በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ መሰረት 23 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተጣራባቸው እንደሚገኝ የጠቅላይ መምሪያ ዕዝ አስታወቀ።

በቁጥጥር ስር የዋሉት ተጠርጣሪዎች ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ፣ ዶክተር ካሳ ተሻገር ዓለሙ፣ ተመስገን አበበ መስፍን፣  ዮሐንስ ንጉሴ ሙጨ፣ በቃሉ አላምረው ሽቱ፣ መላክ አያናው ጥጋቤ፣ ስንታየሁ ቸኮል ደጀኔ፣ ሊቁ እናውጋው ይሁኔ፣ ተመስገን ድልነሳ አለኸኝ፣ ጋሻነህ ላቀ ዘገየ፣ ፈጠነ ወርቄ ባንቴ እና ጌራወርቅ ብዙነህ ሲሳይ ናቸው፡፡

በተጨማሪም አማረ መለስ አከለ፣ ስመኘው አለምነው ሞላ፣ አማኑኤል አዳሙ ተስፋዬ፣ አትርሳው አለም ዘገየ፣ ትንሳኤ ኤልያስ በቀለ፣ ሳሙኤል ለማ ኃ/ገብርኤል፣ አድማሱ ዓለሙ ታየ፣ እታለም ኃ/ማርያም፣ ዮናስ ተ/ማርያም አደሮ፣ አባይነህ ዘውዱ ደመቀ እና ሕይወት ውብሸት ታደሰ በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል መሆናቸው ተገልጿል፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ የጸጥታ ችግር በተከሰተባቸው የአማራ ከልል አካባቢዎች የአገልግሎቶች ሰጪ ተቋማት እንቅስቃሴ ወደ ነበረበት እየተመለሰ መሆኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትሩ ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡

ሚኒስትሩ በሰጡት መግለጫቸው በባህርዳር፣ ደብረማርቆስ፣ ደብረብርሃን፣ ላሊበላ፣ ጎንደር እና ሸዋሮቢት ከተሞች ውስጥ እና ዙሪያ የተሰገሰገው ሃይል መሳሪያ እንዲያስረክብ እና እጁን ለፀጥታ ሃይሎች እንዲሰጥ የተሰጠውን እድል ባለመጠቀሙም እርምጃ ተወስዶበታል ብለዋል፡፡

በተወሰደው እርምጃም አካባቢዎቹ ወደ ሰላማዊ ሁኔታ እንዲመለሱ መደረጉንና ዘራፊ ካሏቸው ሀይሎች ነፃ መውጣታቸውን ተናግረዋል፡፡ ማህበረሰቡም ከመከላከያ ሰራዊቱ ጋር በመሰለፍ አካባቢውን “ከዘረፊ” በመጠበቅ፣ የተዘጉ መንገዶችን በራሱ አቅም በማስከፈት የወደሙ እና የተዘረፉ ንብረቶችን ለመለየት እና ለየባለቤቶቹ እንዲመለሱ ውይይት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡

በስድስቱም ከተሞች የግል እና የመንግስት አገልግሎቶች ሰጪ ተቋማት ወደነበሩበት እንዲመለሱ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን አንስተው በዚህም በአብዛኞቹ ወደ አገልግሎት መመለሳቸውን ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.