ትንታኔ: በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የአንድ ተማሪ ህይዎት የቀጠፈዉ ድልድይ እንዴት ሊፈርስ ቻለ?

ሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዋናውን ግቢ ከቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ጋር የሚያገናኘው ድልድይ በወደቀበት ወቅት ። ፎቶ፡ አዲስ ማለዳ

በምህረት ገ/ክርስቶስ @Mercy23187135

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 02ቀን 2015 /ም፦ በሃዋሳ ዩኒቨርስቲ መስከረም 30 ቀን ሁለት ካምፓሶችን የሚያገናኝ ድልድይ በመደርመሱ አንድ ተማሪ ህይወቱ ሲያልፍ ከ400 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ላይ ቀላልና ከባድ ጉዳት መድረሱ ይታወቃል።

ሃዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ ዝናው ሳርሚሶ ለአዲስ ስታንዳርድ እንደተናገሩት አደጋ በደረሰበት በመጀመርያው ቀን 231 ተማሪዎች ወደ ሆስፒታሉ የመጡ ሲሆን 73ቱ ወድያውኑያ የመጀመርያ እርዳታ አግኝተው ወደ ቤታቸው መሆኑን፣ እንዲሁም 63 ተማሪዎች በሆስፒታሉ ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ጠቅሰው በአጠቃላይ 11 ተማሪዎች በጥሩ ሁኔታ ቀዶ ጥገና ተደርጎላቸዋል ብለዋል።

ከዚህም ከ80 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ሆስፒታሉ በተጎጂዎች ብዛት ቁጥር ምክንያት ከአቅም በላይ ስለሆነበት ወደ ሌሎች ሆስፒታሎች እንዲሄዱ ተደርገዋል ሲሉ አቶ ዝናው አክለው ገልጸዋል። በተጨማሪም የተጎጂ ተማሪ ወላጆች በሆስፒታሉ አስፈላጊ ጥየቃ እያደረጉ ነው ተብለዋል።

አዲስ ስታንዳርድ ይህንን በተመለከተ የሃዋሳ ዩኒቨርስቲ የውጭ ግንኝነት ዋና ኃላፊ ዶ/ር አመቤት በቀለ  በበኩላቸው ጉዳቱ የደረሰው ከዋናው ግቢ ወደ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሲሸጋገሩ ሁለቱን ግቢዎች የሚያገናኘው ድልድይ መሸከም ከሚችለው አቅም በላይ ተማሪዎች ሲወጡበት በመውደቁ ነው ብለዋል።

ድልድዩ የተሰራበት አላማ ሁለቱም የዩኒቨርስቲ ግቢዎች የሚከፍላቸው ትልቅ መንገድ ሰላለ ተማሪዎች ደህንነታቸው በተጠበቀ ከአንደኛው ካምፓስ ወደ ሌላኛው ካምፓስ እንዲሸጋገሩበት የተሰራን እንጂ በአንዴ በዙ ሰዎች የመሸከም አቅም የለውም ተብለዋል።

ከዩኒቨርስቲው የተገኘው መረጃ እሚያመላክተው ከሆነ ቁጥራቸው 451 የሚሆኑ ተማሪዎች ላይ አደጋ መድረሱን በብዙ ተፈታኝ ተማሪዎች ላይ አለመረጋጋት ፈጥሯል። ይህንን በተመለከተ የዩኒቨርስቲው ከፍተኛ አመራሮች በዩኒቨርስቲ ቅጥር ግቢ በመገኘት የማረጋጋት ስራ የሰሩ ሲሆን የተማሪዎች ፍቃድና ዝግጁነት በመጠየቅ ወደ ፈተና እንዲመለሱ ተደርገዋል ሲሉ ዋና ዳይሪከተሯ ገልጸዋል።

ባጋጠመው ድንገተኛ አደጋ ምክንያት በዋና ግቢ ሚገኙ ተፈታኞች ሙሉ ለሙሉ የመጀመርያ ቀን ፈተና ያልወሰዱ ሲሆን በቴክኖሎጂ ግቢ ሚገኙ ተፈታኞች ከሰአት በኋላ የሚሰጠውን ፈተና ሊወስዱ ችለዋል። ይህም ከትምህርት ሚኒስቴርና ፈተናዎች ድርጅት በመነጋገር የሚፈተኑበት ሁኔታ እንደሚመችላቸው ተገልጸዋል።

ድልድዩ የዲዛይን ስራው በዘለቀ በላይ አርክቴክት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የተሰራ ሲሆን የድልድዩ ግንባታ ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ የማማከር ስራ ሰርተዋል

በተጨማሪም የትምህርት ሚኒስርቴ ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በሃዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል በመገኘት ጉዳት የደረሰባቸውን ተማሪዎች መጎበኘታቸው ከዩኒቨርስቲው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ስለድልድዩ ያለው መረጃ

ድልድዩ የዲዛይን ስራው በዘለቀ በላይ አርክቴክት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የተሰራ ሲሆን የድልድዩ ግንባታ ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ የማማከር ስራ የሰሩ ሲሆን፤ የድልድዩ የኮንስትራክሽን ስራም በዛምራ ኮንስትራክሽን እንደተሰራ ከዩኒቨርስቲው የተገኘ መረጃ ያመላክታል።

ድልድዩ በ2007 መጨረሻው አመት ተሰርቶ የተጠናቀቀ ሲሆን ከስምት አመት በላይ ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አገልግሎት ሲሰጥ ቆይተዋል ነው የተባለው።

የድልድዩ የጎኑ ስፋት 2ሜ ከ 50 ሳሜ ሲሆን ርዝመቱም 36 ሜትር እንደሆነ ተጠቁሟል።

በሃዋሳ ዩኒቨርስቲ የግንባታ ፕሮጀክት ጸህፈት ቤት  ሃላፊ የሆኑት አቶ ዮርዳኖስ ዮካሞ በበኩላቸው በቅርብ ግዜ ወደ ተቋሙ መቀላቀላቸው ገልፀው ድልድዩ እስከምን ያክል ክብደትና መጠን እንደሚሸከም እንደሚችል በዩኒቨርስቲው ያለው መረጃ በጥልቀት እንደማያመላክት ለአዲስ ስታንዳርድ አስታውቀዋል።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሲቪል ምህንድስና አስተማሪ የሆኑት ፐሮፌሰር አበበ ድንቁ ለአዲስ ስታንዳርድ እንዳሉት ከሆነ ስለ ጉዳዩ ድምዳሜ ከመደረሱ በፊት ድልድዩ ከዲዛይኑ ጀምሮ ፤ የቴክኒካል ስራው እሰኪሰራ ድረስ ያለው ሂደት ችግር ሊኖረው ስለሚችል ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ ለችግሩ መንስኤ ሊሆን የቻለውን ነገር ጥናት ማደረግ አለበት ብለዋል።

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.