ዜና፡ ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ አስፋው “ሁከት እና ብጥብት በማስነሳት ወንጀል” ተጠርጥሮ  በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገለፀ፤ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው በባህርዳር በፀጥታ አካላት ተይዞ ተወስዷል

በብሩክ አለሙ @Birukalemu21 እና በሚሊዮን በየነ @millionbeyene

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 5/ 2015 ዓ.ም፡- “ኢትዮ ሰላም” የተሰኘ የዩቱዩብ ቻናል መስራች ጋዜጠኛ እና የፖለቲካ ትንታኔ በመስጠት የሚታወቀው ቴዎድሮስ አስፋው በዛሬው እለት ከመኖሪያ ቤቱ በፀጥታ ሀይሎች “ሁከት እና ብጥብት በማስነሳት ወንጀል ተጥርጥረሃል” በሚል ተይዞ መወሰዱን ባለቤቱ እና እናቱ ለአዲስ ስታንዳርድ ገለፁ፡፡  

የፀጥታ ሀይሎቹ ቴዎድሮስን መኖሪያ ቤቱ ይዘውት ከወጡ በኋላ ወደ መኖሪያ ቤቱ ተመልሰው የፌዴራል መርማሪ ፖሊሶች እስኪመጣ ጠብቀው ቤቱን ከፈተሹ በኋላ ፓስፖርቱን እና የግል ስልኩን ወስደው ሜክሲኮ አካባቢ ወደሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ይዘውት ሄዱ ሲሉ እናቱ ወ/ሮ አለም ዘውዱ ተናግረዋል፡፡

ባለቤቱ ወ/ሮ እናት ታምራት በበኩሏ በአቶ ቢኒያም መክብብ ትዕዛዝ መሰረት ነው የመጣነው ባሉ ሲቪል በለበሱ ሰዎችና ሁለት ፌዴራል ፖሊስ መውሰዱን ለአዲስ ስታንዳርድ ገልፀዋል፡፡

ቴዎድሮስ አስፋው በፀጥታ ሀይል በቁጥጥር ስር ሲውል ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን የካቲት 7 ቀን 2015 ስምንት ሰዓት አከባቢ ከመኖሪያ ቤቱ በጸጥታ ኃይሎች ተወስዶ መታሰሩን ይታወሳል። ከዘጠኝ ቀናት እስር በኋላ የካቲት 16 2015 በ30ሺ ብር ዋስትና ከእስር ተለቋል፡፡

በተጨማሪም  “አራት ኪሎ ሚዲያ” የተሰኘ የዩቲዩብ መገናኛ ብዙሃን አዘጋጅ እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የውጭና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው በትላንትናው እለት በባህርዳር ከተማ በፀጥታ አካላት ተይዞ መወሰዱን የስራ ባልደረባው ጋዜጠኛ አላዛር ተረፈ ለአዲስ ስታናዳርድ ገልጿል፡፡

ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው ትላንት ሚያዚያ 4 አመሻሽ ላይ በባህርዳር ከተማ ሆምላንድ በሚባል ሆቴል ከሁለት ጓደኞቹ ጋር ተቀምጦ ባለበት ወቅት አንድ የፀጥታ ሀይል ቀርቦ ለጥያቄ ስለምፈልግህ ና ብሎት መውጣቱን እና ወዲያው ቀይ መለዮ ያደረጉ የመከላከያ ሀይሎች በመኪና ይዘውት መሄዳቸውን ጋዜጠኛ አላዛር ገልጿል፡፡

ዳዊት ባህርዳር የሄደው መጋቢት 10 ቀን የምንሰራበት ቁሳቁስ በመዘረፉ ለጊዜው የምንሰራበት ምቹ ሁኔታ ስላልነበር ለእርፍትና በዛውም ከጓደኞቹ የማቴርያል ድጋፍ ለመግኘት ነበር ሲል የገለፀው ባልደረባው ከመንግስት በኩል ስራችንን በአግባቡ እንዳንሰራ የተለያዩ ተፅዕኖዎች ሲደረስብን ነበር ሲል ገልጿል፡፡

ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው ከዚህ በፊት በአል አይን፣ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት፣ ራዲዮ ፋና፣ ኢትዮ ኤፍ ኤም፣ ኢቢኤስ ቴሌቪዥን፣ ኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ላይ ለበርካታ አመታት በጋዜጠኝነት ሲሰራ የነበር ሲሆን አሁን ላይ ከጋዜጠኛ አላዛር ተረፈ ጋር በመሆን አራት ኪሎ የተሰኘ የዩቲዩብ መገናኛ ብዙሃን በመመስረት በመስራት ላይ ይገኛል፡፡

ሁለት ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ብቻ ከስድስት በላይ ጋዜጠኞች በፀጥታ ሀይሎች ቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡  ኢትዩ ንቃት የተሰኘው ዩትዩብ ቻናል መስራች እና ባለቤት፣ የፖለቲካ ተንታኝ መምህር እና ጋዜጠኛና መስከረም አበራ ሚያዚያ 1  ወደ 12 ሰዓት አካባቢ በፌዴራል ፖሊስ አባላት እና ሲቪል በለበሱ በደህንነት አካላት በቁጥጥር ስር ውላለች፡፡

የየኔታ ትዩብ ጋዜጠኛ ገነት አስማማው ባሳለፍነው ሳምንት ሃሙስ እለት በቁጥጥር ስር መዋሏ ይታወቃል፡፡ በቁጥጥር ስር ካዋሏት ፀጥታ አካላት ጋር የነበረው ንግግር በስልክ ተቀድቶ በማህበራዊ ሚዲያ በስፋት እየተሰራጨ የሚገኝ ሲሆን ከድምፁ መረዳት እንደሚቻለው በጋዜጠኛዋ ላይ ስድብ እና ድብደባ ተፈጽሞባታል፡፡

በተጨማሪም የአማራ ሚዲያ ማዕከል ዋና አዘጋጅ የሆነው አባይ ዘውዱ በተመሳሳይ ባሳለፍነው ሳምንት አጋማሽ መጋቢት 28 2015 ዓ/ም በቁጥጥር ስር የዋለ ሲሆን ዓቃቢ ህግ “ጦር መሳሪያዎችን በመያዝ ተልዕኮ ተቀብሎ የመንግስትስ ከፍተኛ አመራሮችን እና ታዋቂ ሰዎች ላይ እርምጃ ለመውሰድ ሁከትና ብጥብጥ በማስነሳት ህገመንግስቱን እና ህገመንግስታዊ ስርአቱን በሀይል በመናድ ወንጀል ጠርጥሬዋለው ሲል ክስ መስርቶበታል፡፡

ጋዜጠኛ አራጋው ሲሳይ በፌደራል የፀጥታ ሃይሎች ከመኖሪያ ቤቱ መወሰዱን ባሳለፍነው ሳምንት የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ ጋዜጠኛ አራጋው ሲሳይ አዲስ ሚዲያ ኔትወርክ፣ በአማራ ሚዲያ ማዓከል(አሚማ) እና በኢትዮ 251 ኦላየን ሚዲያ ላይ ያገለገለ ሲሆን አሁን ላይ  የግሉ ባቋቋመው ሮሓ ኒውስ ሚዲያ ላይ ሲንቀሳቀስ ነበር፡፡

የአማራ ድምፅ ሚዲያ ዋና አርታኢ ጌትነት አሻግሬ በፌደራል ፖሊስ መያዙን አዲስ ስታነዳርድ የስራ ባልደረባውን እና እህቱን በማናገር መዘገቧ ይታወሳል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.