ዜና፡ የፌደራል መንግስቱ በአማራ ክልል በሚወስደው እርምጃ ምንም አይነት ተሳትፎ የለኝም ሲል የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ገለጸ

አዲስ አበባ፣ ነሃሴ 8/2015 ዓ.ም፡- የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ነሐሴ 7 ቀን 2015 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ የፌዴራል መንግስት በአማራ ክልል ላይ እየወሰደው ባለው እርምጃ ‘የህወሓት ቀጥተኛ ተሳትፎ አለበት’ መባሉን አስተባብሎ ምንም አይነት አስተዋጽኦ እዳላደረኩም ሲል ገልጿል።

ፅንፈኛ ሀይሎች ሲል በገለጻቸው አካላት ‘የህወሓት ቀጥተኛ ተሳትፎ አለበት’ በሚል የሚነዛው ወሬ መከላከያ ሰራዊቱ በመውሰድ ላይ ባለው እርምጃ እየደረሰባቸው ላለው ሽንፈት የትግራይን ህዝብ ሰበብ ለማድረግ ነው ሲል ተችቷል።

የፌዴራል መንግስት በነዚህ ሀይሎች ላይ እየወሰዳቸው ላሉ እርምጃዎች የትግራይም ሆነ የሌላ ወገን የተለየ ድጋፍ ያስፈልገዋል ብለን አናምንም ያለው መግለጫው ይሁንና የፕሪቶሪያውን ስምምነት ለማፍረስ የሚቋምጡ ፅንፈኛ ሀይሎችና አጋሮቻቸው የሚደርጉትን ዘመቻ ለማክሸፍ ከፌዴራል መንግስት ጎን እንደሚቆም አመላክቷል።

አሁንም ቢሆን የትግራይ ህዝብ ሁሉም ችግሮች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ያለው ቁርጠኛ አቋም እንደተጠበቀ ነው ብሏል።

የፕሪቶርያው ስምምነት በተሟላ መልኩ ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት በአማራ ክልል በኩል ይነሱ የነበሩ ከሕግም ከአመክንዮም ጋር ያልተያያዙ ጥያቄዎችን ሰከን ባለ መንገድ ለመፍታት በፌዴራል መንግስቱ ይደረጉ የነበሩ ጥረቶችን ለማገዝ የትግራይ ጊዝያዊ አስተዳደር የሚቻለውን ሁሉ ሲያደርግ መቆየቱን በመግለጫው ጠቁሟል።

የፕሪቶሪያ ስምምነት ተግባራዊ እንዳይደረግ የነበረው ዳተኝነት በስተመጨረሻ በክልሉ የሚገኙ ፅንፈኞችና አጋሮቻቸው ትግራይ ላይ አሰበዉት የነበረውን የጥፋት አላማ የፕሪቶሪያ ስምምነት እንዳከሸፈባቸው የጠቆመው መግለጫው ይህም በዚህም ሳቢያ እነዚህ ሀይሎች በአደባባይ እንዲያማርሩ ከማድረጉም በተጨማሪ ከፌዴራል መንግስት ጋር ቀጥተኛ ጦርነት ውስጥ የገቡበት ሁኔታ መፍጠሩን አስታውቋል። እነዚህ ሀይሎች ፀረ ፕሪቶሪያና ፀረ ትግራይ አቋማቸውን በግልፅ በማራገብ ላይ ይገኛሉ ሲል ገልጿል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.