ዜና፡ የኤርትራ ጦር ከኢትዮጵያ አለመውጣቱን አሜሪካ አስታወቀች

በጥምቀት በዓል ዋዜማ ከሽሬ ከተማ የወጡ ፎቶዎች የኤርትራ ጦር በከተማው ውስጥ እንዳለ ያሳያሉ። ፎቶ: ሃፍቶም በርሄ

አዲስ አበባ፣ጥር 22/ 2015 ዓ.ም፡– ባሳለፍነው ሳምንት መገባደጃ በናይሮቢ ጋዜጣው መግለጫ የሰጡት በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአሜሪካ አምባሳደር ሊንዳ ቶማስ የኤርትራ ሰራዊት ከኢትዮጵያ አለመውጣቱ ገልጸዋል። የኤርትራ ወታደሮችምንም እንኳን ወደ ድንበር አከባቢ መንቀሳቀሳቸው ቢታወቅም አሁንም በኢትዮጵያ ምድር አሉ ሲሉ መግለጻቸውን የጠቆመው ሮይተርስ የዜና ወኪል ለቀው እንዲወጡ መጠየቃቸውንም አስታውቀዋል ብሏል።

ከሊንዳ ቶማስ ገለጻ ቀናት በፊት በጥር 22/ 2015 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ የውጭ ግንኙነት እና ወታደራዊ ትብብር ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ላደረጉ ለተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች፣ የአፍሪካ ህብረት ተወካዮች እንዲሁም አለምአቀፍ ተወካዮች በሰላም ስምምነቱ ትግበራ ዙሪያ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት በትግራይ ክልል ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ውጭ በግዳጅ ላይ ያለ ሌላ የፀጥታ ሀይል የለም ሲሉ አስታውቀው ነበር። ሜጄር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ የተፈጠረው የሰላም ስምምነት ለሀገራችን ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው ሀገራትም የሰላም አየር ለመተንፈስ አስችሏል ማለታቸውም ይታወሳል።

በሌላ በኩል በጉዳዩ ዙሪያ የትግራይ ክልል ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ በማህበራዊ የትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ የኤርትራ ሀይሎች አለመውጣታቸውን አመላክተዋል። ሜጄር ጄኔራል ተሾመ ገመቹ የሰጡት አስተያየት ቢያንስ በሁለት ምክንያቶች አሳሳች ነው ያሉት አቶ ጌታቸው አበረታች የሆኑ ምልክቶች ቢኖሮም በሺዎች የሚቆጠሩ የኤርትራ እና የአማራ ኃይሎች ትግራይ ውስጥ አሁንም ይገኛሉ፣ አልወጡም ብለዋል። በተጨማሪም በስምምነቶቻችን መሰረት ጉዳዩን አጣርቶ፣ አረጋግጦ መግለጽ የሚገባው የአፍሪካ ህብረት ተቆጣጣሪ ቡድን ነው ሲሉ ገልጸዋል።

ከሳምንት በፊት የአሜሪካን መንግስት የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ባወጣው መግለጫ የኤርትራ ጦር ሰራዊት በመውጣት ላይ መሆኑን ጠቁሞ ነበር። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ከጠ/ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋር በስልክ መወያየታቸውን ባስታወቀበት መግለጫው የኤርትራ ጦር ከትግራይ በመውጣት ላይ መሆኑን እና ይህንንም የአሜሪካ መንግስት በአወንታዊነቱ ይመለከተዋል ሲል ገልጾ ነበር። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.