ዜና: የአዲስ አበባ እና የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤቶች በጎንደር ከተማ በተፈጸመው ጥቃት ጥፋተኞቹ ለህግ እንዲቀርቡ ጠየቁ

ጌታሁን ጸጋዬ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዚያ 19፣2014 ዓ.ም :- የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ዛሬ ማለዳ ላይ ባወጣው መግለጫ በትላንትናው እለት ሚያዚያ ማክሰኞ ቀን 18/2014 ከሸይኽ ከማል ለጋስ (ረሂመሁላህ) የቀብር ስነ ስርአት ላይ ደረሰው ጥቃት የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 21 መድረሱን አስታውቆ ቀድሞ “በታቀደና በተቀናጀ መልኩ በሙስሊሙ ላይ ከባድ የሆነ ጭፍጨፋ”  ብሎታል። አማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤትም ባወጣው መግለጫ መንግስት በክልሉ በሙስሊሙ ማህበረሰብ እና ንብረታቸው ላይ እየደረሰ ያለውን ያልተቋረጠ ጥቃት በማቆም ወንጀለኞች ለህግ እንዲቀርቡ ጠይቋል። ክስተቱ በርካቶችን ያስቆጣ ሲሆን በአዲስ አበባ የሚገኙ ሙስሊሞች ዛሬ በታላቁ አንዋር መስጂድ የተቃውሞ ሰልፍ አካሂደዋል።

በአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የወጣው መግለጫ “በዚህ የደቦና የመንጋ ጭፍን አስተሳሰብና ሀገርን አውዳሚ በሆነ ተግባር በህዝበ ሙስሊሙ ላይ ከፍተኛ የሆነ ሙስሊም ጠልነትን በግልፅ በሚያሳይ መልኩ መስጂዶች ተቃጥለዋል፣ከፍተኛ የሆነ የንብረት ማውደም ተግባር ተፈፅሟል” ያለ ሲሆን  ሴቶች መደፈራቸውንም ጠቅሷል። ምክር ቤቱ መንግስትን፣ የአማራ ክልል ሚዲያዎችን እና አንዳንድ የፖለቲካ አመራሮች በጉዳዩ ላይ የሰጡት መግለጫ “በፅንፈኞች በመስሊሙ ላይ የተቃጣውንና የ21 ሙስሊሞችን ህይወት የቀጠፈውን ወንጀል የእርስ በርስ ግጭትና በሀሰት በድንበር ምክንያት የተፈጠረ ነው በማለት ያወጡት መግለጫ ሀገርን ለማፈራረስ ላቀዱ ሰዎች ሽፋን ከመሆኑም ባሻገር ምክር ቤታችንንም ሆነ ህዝበ ሙስሊሙን በከፍተኛ ደረጃ አሳዝኗል”  ሲል ቅሬታውን ገልጿል ። መንግሥት የጉዳቱን ክብደት በግልፅ እንዲገልጽና አጥፊዎችን ለህግ እንዲያቀርብ ምክር ቤቱ ጠይቋል። መላው ህዝበ ሙስሊም ጉዳዩን በሰላማዊ መንገድ እንዲያስተናግድና ወደፊትም መሰል ጥቃቶች እንዳይፈጸሙ በትኩረት እንዲከታተል ጥሪ አቅርቧል። 

አማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት በበኩሉ በጎንደር ከተማ ትናንት በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ የደረሰውን ጥቃት በማውገዝ ዛሬ መግለጫ አውጥቷል። ምክር ቤቱ መሰል ጥቃቶችን ለመከላከል ስትራቴጂ ነድፎ ወደፊትም ሙስሊም ማህበረሰቦችን እንደሚያደራጅ አስታውቋል። በተጨማሪም በመላው አለም የሚገኙ ሙስሊም ማህበረሰቦች ጥቃቱን በማንኛውም መንገድ እንዲያወግዙ እና የቀጣዩ የመፍትሄ አካል እንዲሆኑ ጥሪ አቅርቧል።

በመግለጫው መሰረት ሙስሊሙ ማህበረሰብ እየደረሰበት ያለው ዘረፋ፣ እንግልት እና እንግልት ሊያሳስባቸው የሚገቡ ሌሎች የሀይማኖት አባቶች በሙስሊሞች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት እንዲያወግዙና ተከታዮቻቸውን እንዲመክሩም አሳስቧል።

የአማራ ክልል ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ደሳለኝ ጣሰው በትናንትናው እለት ጉዳዩን አስመልክቶ ባደረጉት ገለጻ  ፣ ለቀብር የወጡ  ሃዘንተኞች ከመስጊድ አጠገብ ከሚገኝ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ድንጋይ እየሰበሰቡ ነው በማለት በቡድን የተደራጁ ሰዎች   በህዝቡ ላይ በድንጋይ ጥቃት መሰንዘራቸውን አስረድተዋልል።“በግለሰቦች መካከል የተፈጠረው ግጭት ወደ ቡድን ግጭት የማደግ አዝማሚያ አሳይቷል” ብለዋል አቶ ደሳለኝ።

የአካባቢው ሚሊሻዎችን ጨምሮ ፣የክልሉ ፖሊሶች፣ አድማ በታኞች እና መሰል የጸጥታ ሃይሎች ሁከቱን ለመቆጣጠር መሞከራቸውን እንዲሁም፣ ወጣቶች እና የአካባቢው የሀገር ሽማግሌዎች የጸጥታ ሃይሎችን ለመርዳት ያረጉትን ጥረት ያወሱትት አቶ ደሳለኝ የጸጥታው ሃይል “ሁኔታውን መቆጣጠር” በሚቸልበት ቁመና ላይ ይገኛል ብለዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.