ዜና- የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ቅርንጫፍ በአሶሽየትድ ፕረስ ጋዜጠኞች ላይ ዘጠኝ የምርመራ ቀን ፈቀደ





የአሶሽየትድ ፕረስ ጋዜጠኛ አሚር አማን እና የካሜራ ባለሙያው ቶማስ እንግዳ

በማህሌት ፋሲል @MahletFasil

አዲስ አበባ፣ የካቲት 15፣ 2014 – የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ቅርንጫፍ የግዜ ቀጠሮ ችሎት ዛሬ የቀረቡት  የአሶሽየትድ ፕረስ ጋዜጠኛ አሚር አማን እና የካሜራ ባለሙያው ቶማስ እንግዳ ላይ ፖሊስ ምርመራን ስላልጨረስኩ 14 ተጨማሪ ቀን ይሰጠኝ ሲል ችሎት ጠይቋል። ፍርድ ቤቱም 9 የምርመራ ቀናት ፈቅዶለታል።

መርማሪ ቡድኑ ጋዜጠኞቹ በህዝብ ተወካዩች ምክር ቤት አሸባሪ ተብሎ ከተፈረጀው የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት (OLA) አመራሮችን በስልክና በአካል በመሄድ ታጣቂዎቹን በማነጋገርና በመቅረጽ ለተለያዩ የአውሮፓ አገራት በመላክ ኢትዩጵያ ላይ የተሳሳተ አመለካከት እንዲኖር ለማድረግ ሲሞክሩ ነው የያዝኳቸው ብሏል።

በታህሣሥ ወር አጋማሽ ላይ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊትን (ኦነግ ሸኔ) በአለም አቀፍ ደረጃ ያስተዋውቃሉ ያላቸውን ሁለት ጋዜጠኞች እና አንድ ካሜራማን ማሰሩን አስታውቋል። መግለጫው “በምዕራብ ሸዋ ዞን ውስጥ ሸኔን  ለማስተዋወቅ ብዙ ገንዘብ የተከፈላቸው ጋዜጠኞች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሆነው እየተመረመሩ ነው” ብሏል ። በእስር ላይ በነበረበት ወቅት ከገዥው ፓርቲ ፋናቢሲ ጋር ሲሰራ የነበረው አዲሱ ሙሉነህ ከእስር ተፈቷል።

መርማሪ ፖሊስ በተጨማሪም ተጠርጣሪዎቹ በእስር በነበሩበት ወቅት የተለያዩ ስራዎችን ሰርቼያለው ሲል ለችሎት ያስረዳ ሲሆን የተከሳሽ ቃል መቀበሉን ፣ከተጠርታሪዎች እጅ የተያዙ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ለብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት ምርመራ እንዲደርግ መላኩን ፣እንዲሁም መስሪያ ቤቱ ተጠርጣሪዎቹን በተመለከተ የቴክኒክ ማስረጃ እንዲልክ መጠየቁን ያስረዳ ሲሆን በቀጣይ የላኩዋቸውን መረጃዎች መሰብሰብ ስለሚቀረኝ 14 ቀን ይሰጠኝ ሲል ጠይቋል።

የተከሳሽ ጠበቆች በበኩላቸው ፖሊስ የጠየቀው ቀን መሰጠት የለበትም፣ ደንበኞቻችን ስራቸውን በመስራታቸውና ጋዜጠኛ በመሆናቸው ነው የታሰሩት ያሉ ሲሆን ከወራት በፊት ፖሊስ በመንግስት ሚዲያ በተላለፈው ዘጋቢ ፊልም ላይ ክስ ለመመስረት ዝግጅት ላይ ነበር ብለዋል።  አሁን ፖሊስ የጠየቀው ይህን ያህል ቀን አግባብ አይደለም በማለት ተከራክረዋል።  

የሁለቱን ክርክር ያዳመጠው ፍርድ ቤቱ ለመርማሪ ፖሊስ 9 ተጨማሪ ቀን ሰቷል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.