ዜና: ከኦሮሚያ ክልል የተፈናቀሉ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች ወደ አማራ ክልል እየገቡ ነው፣ ተ.መ.ድ

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ቶሌ ቀበሌ ሰኔ በሰኔ ወር ከደረሰው ጭፍጨፋ የተረፉ ተፈናቃዮቹ መካከል በደብረ ብርሃን ከተማ በጊዜያዊ መጠለያ ካምፖች ውስጥ ተጠልለው የሚገኙ። ፎቶ የተነሳው በሐምሌ ወር ነው ፎቶ ፣ ሀሩንቲዩብ ሚዲያ

አዲስ አበባ ጥቅምት 08/2015 ዓ/ም፣ በኦሮሚያ ክልል በተለይም በወለጋ ዞኖች እየተካሄደ ባሉ ግጭቶች የተነሳ በርካታ በአካባቢው ይኖሩ የነበሩ ሰላማዊ ሰዎች ወደ አማራ ክልል መፈናቀል መቀጠላቸውን በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ እርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ ዲስ በለቀቀው ዘገባ ተናግሯል። ይሁንና ሪፖርቱ ምን ያህል ሰላማዊ ዜጎች ተፈናቅለው ወደ አማራ ክልል እንደደረሱ አልገለጸም።

በዚህም መሠረት በርካታ የተፈናቀሉ ሰላማዊ ሰዎች ወደ ጎጃም፣ ሰሜን ሸዋ፣ ደቡብ ወሎ፣ ዋግ ኽምራ ዞኖች እንዲሁም በባህር ዳርና በደብረ ብርሃን ከተሞች መጉረፋቸውን የዞኑ ባለስልጣናት እና ግብረሰናይ አጋሮች አረጋግጠዋል ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ እርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ በትናንትናው እለት ባወጣው አጭር ዘገባ ገልጿል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በሰሜን ወሎ ዞን የሚታየውን የፀጥታ ሁኔታ መሻሻል ተከትሎ ከሳምንታት በፊት በጦርነት የተፈናቀሉ ወደ 100 ሺህ የሚጠጉ አብዛኞቹ ከራያ ቆቦ ወረዳ የተፈናቀሉ እና በ17 መጠለያ ቦታዎች እና በመርሳ ከተማ ከሚገኙ ነዋሪ ማህበረሰብ መካከል ተጠልለው የቆዩ ዜጎች ወደ ትውልድ ቀያቸው መመለስ ጀምረዋል ሲል ዘገባው ጨምሮ ገልጿል።

አብዛኛዎቹ እነዚህ ተፈናቃዮች ወደ ቤታቸው የተመለሱ ሲሆን ጥቂቶች ደግሞ ከአስተናጋጁ ማህበረሰብ ጋር ተጠልለው ይገኛሉ።

ቢሆንም በእነዚህ አካባቢዎች ያሉ አብዛኛዎቹ መሰረታዊ አገልግሎቶች የማይሰሩ ወይም የተበላሹ እንደሆኑ ተገምቷል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.