ዜና ትንታኔ: በአማራ ክልል የፀጥታ መዋቅሩ በትግራይ ሃይሎች የሚሰነዘር ጥቃት፣ ስርዓት አልበኝነት እና ህገ-ወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውር ለመግታት ዝግጁ እንዲሆን ተጠየቀ

አዲስ አበባ ግንቦት 6፣ 2014 ፦ የአማራ ክልል የጸጥታው ምክር ቤት በክልሉ ያለውን ሰላምና ጸጥታ ሁኔታ መገምገሙን ገልጾ የጸጥታ መዋቅሩና የክልሉ ህዝብ “በአማራ ክልል ላይ ዳግም ጦርነት አውጀዋል” ባላቸው የትግራይ ሃይሎች የተቃጣበትን ወታደራዊ ጥቃት ለመከላከል እንዲዘጋጅ አሳስቧል። 

ምክር ቤቱ  የክልሉን ሰላምና ፀጥታ አደጋ ላይ የሚጥሉና የክልሉን መንግስት እያዳከሙ ያሉ “ስርአት አልብኝነት፣ህገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች፣ የተደራጁ እና ያልተደራጁ ታጣቂዎች”   እየተባባሱ በመምጣታቸው “ለክልሉ ሰላምንና ደህንነት ስጋት እንዲሁም ክልሉን እያዳከሙ” ነው ብሏል ። 

የጸጥታ ምክር ቤት በየደረጃው የጸጥታ ግብረ ሀይል አቋቁሞ ህገ-ወጥነትን ለመቆጣጠርና ህግን ለማስከበር ተገቢ ነው ያላቸውን ህጋዊ ርምጃ እንዲወስድ አቅጣጫ ማስቀመጡን የገለፀ ሲሆን  “የክልሉ ህዝብ፣ ወጣቶች ፣ የገጠርና የከተማ ኗሪዎች ሰላምና ደህንነታችን ለመጠበቅ እና የውስጥ አንድነታችን ለማጠናከር የፀጥታ መዋቅሩ በሚወስደው እርምጃ ሁሉ ተባባሪ እንሁን” ሲል ጥሪ አቅርቧል፡፡

የምክር ቤቱ መግለጫ የወጣው በአሁኑ ሰዓት በአማራ ክልል አስተዳደር ውስጥ የተካተቱትን የምእራብ ትግራይ ቦታዎች እና በማእከላዊ ትግራይ የምትገኙውን ራማን ጨምሮ ትግራይ እና ኤርትራን በሚያዋስኑ አካባአቢዎች እያገረሹ የመጡ ግጭቶች ካልተረጋገጡ ዘገባዎች እየወጡ ባለበት ውቅት ነው። ዘገባዎቹ በትግራይ አመራሮች ተቀባይነት የላቸውም። የትግራይ ፕሬዝዳንት አማካሪ እና የህወሓት ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ ከሠራዊታቸው ጋር እየተካሄደ ያለውን ወታደራዊ ግጭት አስመልክቶ የተሰራጨውን ዘገባ ያስተባበሉ ሲሆን “በእርግጥ በትግራይ አንዳንድ አካባቢዎች በሰላማዊ ዜጎች ላይ በጅምላ በኤርትራውያን የተኩስ ጥቃት ደርሶበታል” ብለዋል።

ዋዜማ ራዲዮ በግንቦት 4፣ 2014 ዓ.ም.  የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድረር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል (ዶ/ር) የትግራይ ህዝብ ለ”መጨረሻው የትግል ምዕራፍ” መዘጋጀት እንዳለበት ማሳሰባቸውን ዘግባለች።  ርዕሰ መስተዳድሩ ከፌደራል መንግስት ጋር ችግሮችን በዲፕሎማሲ ለመፍታት ሲደረግ የነበረው ጥረት አለመሳካቱን በዚህ ሳምንት በክልሉ ባደረጉት ስብሰባ ለትግራይ ሕዝብ ማሳወቃቸውን ተከትሎ የመንግስት ሚዲያዎች እንዲሁም የክልል እና የህዝብ መገናኛ ብዙሃን የትግራይ ሃይሎች ዳግም ጥቃት ለመፈፀም መዘጋጀታቸውን ሲዘግቡ ቆይተዋል።

የአማራ ክልል የጸጥታው ምክር ቤት የክልሉን ሰላምና ጸጥታ ሁኔታ ከገመገመ በኋላ “ህወሓት የትግራይን ህዝብ ለመዋጋት በማነሳሳት በአማራ ክልል ላይ ጦርነት አውጇል ” ብሏል።

በተመሳሳይ የወልቃይት የማንነት ኮሚቴ አመራር እና የምእራብ ትግራይ አስተዳዳሪ የሆኑት ኮሎኔል ደመቀ የምዕራብ ትግራይ ዋቢ በወልቃይት ጠገዴ ላይ ወታደራዊ ጥቃት ለመሰንዘር ተዘጋጅተዋል ያላቸውን የትግራይ ታጣቂዎች የሚሰነዝሩትን ጥቃት ለመከላከል በክልሉ የሚገኙ ሁሉም ህዝቦች እንዲሁም የፌዴራል እና የክልል መንግስታት አካባቢውን እንዲከላከሉ ጥሪ አቅርበዋል። “ተመጣጣኝ ዝግጁነት መኖር አለበት; ጠላት ዝግጅቱን አጠናቆ የጦርነት ከበሮ እየመታ  ነው” ያሉት ኮሎኔል ደመቀ ጉዳዩ በፌዴራልም ሆነ በክልል መንግስታት ተገቢውን ትኩረት ሊሰጠው እንሚገባ ገልጸው ከሁሉም በላይ ከመንግስት ጎን መቆም ያለበት ህዝብ ነው ብለዋል።

ሕገወጥነት እና የጦር መሣሪያ መስፋፋትን በተመለከተ

የአማራ ክልል የጸጥታ ምክር ቤት “ለህግ ማስከበር መዳከም” ዋና ተግዳሮቶች ናቸው ያላቸው ጉዳዮች ላይ በሰፊው ተወያይቷል። ።ምክር ቤቱ ሰሞኑን ባደረገው በየደረጃው ባሉ የህዝብ ውይይቶች ላይ “የአማራን ውስጣዊ አንድነት ለማዳከምና ለጠላት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚንቀሳቀሱ የተደራጁና ያልተደራጁ ኃይሎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን እና የጸጥታ ስጋት መሆኑን  አመልክቷል” ብሏል።.

ምክር ቤቱ በስም ሳይጠቅስ “እነዚህ ኃይሎች በእምነት፣ በፖለቲካ፣ በብሔር ህዝባችን እየከፋፈሉ የአማራን የውስጥ አንድነት በማዳከም ለጥቃት ተጋላጭ እንዲሆን የሚያደርጉት ሙከራ በአጭር ካልተቀጨ በህዝባችንና በክልላችን ሰላምና ደህንነት ላይ ዘላቂ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል ድምዳሜ ላይ ደርሷል” ብሏል ፡፡

በተጨማሪም ምክር ቤቱ እነዚህን ሃይሎች የህገ-ወጥ ንግድን ከማስፋፋት፣  ሰው ሰራሽ የምርት እጥረት ከመፍጠር፣ የኑሮ ውድነት ከማባባስ፣ ፣ ምርትን ለጠላት በኮንትሮባንድ አሳልፈው ከመላክ፣ የህዝብን ሃብት ከመዝረፍ ጋር አያይዞ ወቀሳ ያቀረበ ሲሆን ድርጊቶቹም  የዜጐችን ነጻ እንቅስቃሴ የሚገድቡ እና “ለክልሉ እያደጉ የመጡ የፀጥታ ስጋት” ናቸው ሲል በመግለጫው አሳታውቋል።  በተጨማሪም “በተለያዩ የክልሉ አካባቢወች እየተስፋፋ የመጣው ህገ-ወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውር የክልሉን ሰላምና ደህንነት ስጋት ውስጥ እየጣለ ይገኛል” ብሏል፡፡ አክሎም መሳሪያን ለመሞከር በሚል በሃዘንና በደስታ ላይ በግዴለሽነት በሚተኮስ ጥይት የንጹሀን ህይወት እየቀጨ መምጣቱን የጸጥታ ምክርቤቱ አመልክቷል፡፡

“ህገ-ወጥነትና ስርዓት አልበኝነት ስር እየሰደደ በመምጣቱ ህገ-ወጥ ታጣቂዎች በሚያደርጉት ያልተገባ እንቅስቃሴ የክልሉን ልማቶች እያዳከመ፤ የዜጎችን ነጻ እንቅስቃሴ እየገደበ ፤ የኢንቨስትመንት እድሎችን እየዘጋ፣ የተፈጠረውን የስራ ዕድል እያጠፋ፣ ለቀጣይ ልማትም እንቅፋት በመሆንና በአጠቃላይ የአማራን ክልል ልማት በአደገኛ ሁኔታ እየተፈታተነ እንደሚገኝ” በአጽንኦት እንደተመለከተው አስታውቋል። 

“እነዚህ ህገ-ወጥ ተግባራት በከተማም ሆነ በገጠር በአጭር ጊዜ ማረም ካልተቻለ የአማራ ክልል ልማት የሚያስቀጥል ሳይሆን የነበረውንም የሚያመክን የህገ-ወጥነትና የስርዓት አልበኝነት መናኸሪያ የሚያደርግ”  ነው ሲል የተናገርው ምክር ቤቱ  በጦርነቱ ምክንያት ተፈናቀለው የሚገኙ ሰዎች በአግባቡ ምግብ እንዲያገኙ ተደርጎ  ወደ ቀያቸው በጊዜ መመለስ ካልተቻለ የፀጥታና ሰብአዊ ቀውስ እንደሚያስከትል ግምገማውን አስታውቋል፡፡ 

ከዚህ ጋር በተያያዘም የክልሉ መንግስት “ህዝቡ በተለያዩ ውይይቶች ያነሳቸውን ጥያቄዎች” ተቀብሎ “በየደረጃው የህግ የበላይነትን በማስፈን የህዝቡን ሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ አለበት” ብሎ ያምናል ብሏል።በመሆኑም በየደረጃው የሚገኙ የክልል የጸጥታ መዋቅሮች የክልሉን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ እና ዳግም በትግራይ ሃይሎች የሚደርሰውን ጥቃት “መቀልበስና መከላከል” እንዲችሉ አቅጣጫ ማስቀማጡን ምክር ቤቱ አስታውቋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.