ትንታኔ፡በሸዋ ሮቢት ከተማ ሰላማዊ ሰልፍን ለመበተን የፀጥታ ሃይሎች በተኮሱት ጥይት የህይወት መጥፋትና የአካል ጉዳት ደረሰ

በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ሸዋ ሮቢት ከተማ ። ምስል፡ የሸዋ ሮቢት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ

በጌታሁን ፀጋዬ

ሰኔ 28፣ 2014 ዓ.ም፣ አዲስ አበባ፦ “በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በሸዋ ሮቢት ከተማ የተካሄደውን ሰላማዊ ሰልፍ ተከትሎ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች ላይ የሞትና የአካል ጉዳት ደርሷል” ሲሉ ነዋሪዎች ለአዲስ ስታንዳርድ ተናገሩ። አሁንም ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የታሰሩ እንዳሉም ነዋሪዎች አክለው ተናግረዋል።

በአባታቸው ስም መጠራትን የመረጡት የሸዋ ሮቢት ከተማ ነዋሪ የሆኑት  አቶ ታደስ ለአዲስ ስታንዳርድ እንደተናገሩት የከተማው ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ሐሙስ ሰኔ 21 ቀን 2014 ዓ.ም በወለጋ የአማራ ብሄር ተወላጆች ላይ እየደረሰ ያለውን ግድያ በማውገዝ መንግስት ህገ መንግስታዊ ኃላፊነቱን እንዲወጣ እና በሀገሪቱ ውስጥ ህግና ስርዓት እንዲሰፍን  በሰላማዊ ሰልፍ ጠይቀዋል። 

“ስሜታዊነት ስለነበር በጸጥታ ሃይሎች እና በህዝቡ መካከል አለመግባባት ስለተፈጠረ  ሁኔታው ​​ተባብሷል”  ያሉት እኝህ እማኝ አለመግባባቱን ተከትሎ የፀጥታ ያህሎች ባነሱት ተኩስ  ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች መሞታቸውንና የአካል ጉዳት መድረሱንም  ተናግረዋል

እንደ አቶ ታደስ ገለጻ፣ በማግስቱ የጸጥታ ሃይሎች እና ህግ አስከባሪዎች ቤት ለቤት በመሄድ ተማሪዎችን፣ የፖለቲካ አመራሮችን (የወረዳውን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊን ጨምሮ) እና ሰልፉን በማስተባበር  ተሳትፈዋል ያሏቸውን ግለሰቦች በቁጥጥር ስር አውለዋል። የተከሰተውን እስር ተከትሎም በተመሳሳይ አርብ ሰኔ 22 ቀን የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች እና የከተማዋ ነዋሪዎች እስረኞቹ ወደሚገኙበት ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ እንዲፈቱ ጠይቀዋል።

“ስሜታዊነት ስለነበር በጸጥታ ሃይሎች እና በህዝቡ መካከል አለመግባባት ስለተፈጠረ  ሁኔታው ​​ተባብሷል”  ያሉት እኝህ እማኝ አለመግባባቱን ተከትሎ የፀጥታ ያህሎች ባነሱት ተኩስ  ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች መሞታቸውንና የአካል ጉዳት መድረሱንም  ተናግረዋል።

ሌላው ለአዲስ ስታንዳርድ  ሁኔታውን አስመልክተው ምስክርነታቸውን የሰጡት የከተማው ነዋሪ አቶ ሳህሌ (ስማቸው በተጠየቁት መሰረት  የተቀየረ) “በቁጥራቸው ምን ያህል እንደሆነ ባላውቅም የሞቱት፣ የተጎዱ እና የታሰሩ ነበሩ” ሲሉ የታደስን ሀሳብ አጠናክረውታል። ከአርብ ዕለት አንስቶ ለተከታታይ ሶስት ቀናት የሸዋ ሮቢት ከተማ ከወትሮው በተለየ ፀጥታ ውስጥ እንደነበረች አውስተው፣ የንግድ ድርጅቶች ተዘግተው እንደነበር እና በቀጣይ ምን ሊፈጠር እንደሚችል በመፍራት አብዛኛው ነዋሪዎች በቤታቸው እንደቆዩ አክለዋል።

ዶቼ ቬሌ አማርኛ በበኩሉ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በአማራ ክልል በሰሜን ሰዋ ዞን ሸዋ ሮቢት ከተማ የወለጋውን ጭፍጨፋ በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉን አውስቶ ከሰልፉ በኋላ የታሰሩት ይፈቱልን በሚል በተፈጠረ አለመግባባት በግምት 12 ሰዎች እንደተገደሉ እማኞችን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል

አዲስ ስታንዳርድ ለተጨማሪ ማብራሪያ የከተማውን ከንቲባ ጽህፈት ቤት በስልክ ያናገረች ሲሆን “በአሁኑ ሰዓት ምንም ዝርዝር መረጃ ልሰጥህ አልችልም። ከተማዋ በወረዳው እና ከተማ አስተዳደር ጥምር ኮማንድ ፖስት ስር ናት” በማለት የከንቲባው ጽህፈት ቤት ተወካይ ገልጸዋል።

የከተማው ከንቲባ ጽ/ቤት ባወጣው መግለጫ በተፈጠረው ችግር ምክንያት ለጠፉው የሰው ህይወትና መቁሰል አደጋ ማዘኑን ጠቅሶ  ከተማዋ ወደ ነበረችበት ሰላም እንድትመለስ ከተማ አስተዳደሩ ከቀወት ወረዳና ከሌሎች የጸጥታ መዋቅር እንዲሁም ከሀገር ሽማግሌዎች ጋር በመሆን  ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ መሆናቸውንና ዘላቂ ሰላሟም እንዲረጋገጥ የሸዋሮቢት ከተማ አስተዳደርና የቀወት ወረዳ አስተዳደር ጥምር ኮማንድ ፖስት ማቋቋሙን ገልጿል። አያይዞም  በተቋማትና በከተማዋ ነዋሪዎች ዘንድ መተግበር የሚገባቸውን የአስቸካይ ጊዜ   ክልከላዎችን ያወጀ ሲሆን በከተማዋ  አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙ ተሽከርካሪዎች በተለይም ደግሞ ባጃጅና ሞተር ሳይክል መንቀሳቀስ የሚችሉት ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት ብቻ እንዲሆን፣ ከመንግስት የፀጥታ መዋቅር ውጪ ማንኛውንም አካል የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ እንደማይቻል፣ ማንኛውም የንግድና አገልግሎት ሰጪ ተቋም የስራ እንቅስቃሴ ማድረግ የሚችለው ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2 ስአት ብቻ እንደሆነ፣ከተፈቀደለት የፀጥታ አስከባሪ መዋቅር  ውጪ በቡድንም ይሁን በተናጥል ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት ዉጪ መንቀሳቀስ እንደማይችል፣ በየትኛውም የመንግስት ተቋም የሚሰራ የመንግስት ሰራተኛ በመንግስት የስራ ሰዓት ከስራ ገበታው ዉጪ መገኘት በጥብቅ የተከለከለ እንደሆነ ጠቅሷል። መግለጫውም ሌሎች ክልከላዎች ያካተተ ሲሆን ፣ የመንግስትና የግል አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በተፈቀደላቸው መደበኛ የስራ ሰዓታቸው ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡና ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር እንዳለባቸው የደነገገ ሲሆን  ለከተማዋ ህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል ከላይ የተጠቀሱትን ድንጋጌዎች በማያከብር ግለሰብም ይሁን ተቋም የጥምር ኮማንድ ፖስቱ ህጋዊና ተመጣጣኝ እርምጃ የሚወስድ መሆኑን መግለጫው አሳስቧል።

በምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ ቅዳሜ ሰኔ 18 ቀን ከ200 በላይ አማራዎች በታጣቂዎች መገደላቸውን አስመልክቶ አዲስ ስታንዳርድ ሰፊ ዘገባ ይዛ መውጣቷ ይታወሳል።

ለተጨማሪ ማብራሪያ አዲስ ስታንዳርድ የተባለውን ኮማንድ ፖስት ለማነጋገር ያደረገችው ሙከራ አልተሳካም። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.