ዜና ትንታቴ፡ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ውዝግብ ያስነሳውን የብሄራዊ መልቀቂያ ፈተና ማብራሪያ ጠየቀ

አዲስ ስታንዳርድ ሪፖርተሮች

አዲስ አበባ መጋቢት 10/2014:-የሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ እና ትምህርት ሚኒስቴር በሁለት ዙር የተካሄደውን የትምህርት መልቀቂያ ፈተና ውጤት ይፋ ካደረጉ በኋላ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት እና መቁረጫ ነጥብ ላይ ጥያቄ አቅርቧል። የክልሉ ትምህርት ቢሮም የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤትና መቁረጫ ነጥብ በተመለከተ ከትምህርት ሚኒስቴር ማብራሪያ ጠይቋል።

የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) የ12ኛ ክፍል ፈተና በሁለት ዙር እንዲሰጥ መደረጉንና በመጀመሪያው ዙር የስነ-ዜጋና ስነ ምግባር ትምህርት ከፈተናው ቀን ቀድሞ በመውጣቱና የውጤት ግሽበት በመምጣቱ እንዲሰረዝ መደረጉን ተናግረዋል።

በሁለተኛው ዙር ፈተና ከተፈተኑት 53,997 ተማሪዎች መካከል 28 በመቶው በመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች የሚመደቡ ሲሆን በመጀመሪያው ዙር ከተቀመጡት 554,682 ተማሪዎች መካከል 25 በመቶው በመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚመደቡ ሚኒስቴሩ አስታውቋል።  በጣም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች በዘንድሮው አመት የ12ኛ ክፍል ፈተናን የወሰዱ ሲሆን ይህም የሆነበት ምክኒያት የ 10ኛ ክፍል የማትሪክ ፈተና ባለፈው አመት በመቅረቱ ነው ብለዋል።  በተጨማሪም በትግራይ ያሉ አራት ዩኒቨርሲቲዎች ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች መመደባቸውና ዘንድሮም ይመደቡ የነበሩ ተማሪዎች ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ መደረጉ 48ሺ ተማሪ የቅበላ አቅም አጥተናል ብለዋል።

የፈተና አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ተፈራ ፈይሳ በበኩላቸው ኤጀንሲው ከ20 ሺህ የሚበልጡ ቅሬታዎችን ለግምገማና ለማረም ተቀብሏል ብለዋል።

የአማራ ክልል መገናኛ ብዙሃን በሰሜን ወሎ ዞን ከሚገኙ 42 ትምህርት ቤቶች በስድስት ትምህርት ቤቶች ለትምህርት መልቀቂያ ፈተና ከተቀመጡት 679 ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት መውደቃቸውን የገለፀ ሲሆን ይህም የውጤት አወሳሰዱን ከመደበኛ ስርዓት ውጭ መሆኑን ዘግቧል።እነዚህ ድርጊቶች የተስተዋሉባቸው ትምህርት ቤቶች ጊራና ካሊም ፣ቁል መሰቅ ፣ጉርጉር ደብረሮሃ ፣ሃናሙቃት ደብረሲና እና ከበበው ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መሆናቸውን የክልሉ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

በተጨማሪም የሰሜን ወሎ ዞን ትምህርት መምሪያ ፈተና እና አስተዳደር ባለሙያ  ሙሉ አዳነ እንደገለፁት ዞኑ በጦርነት ውስጥ ከገባ ከ5 ወራት በላይ ያስቆጠረ ሲሆን አሁንም በክልሉ የሚገኙ ተማሪዎች ለፈተና ለመቀመጥ ሙሉ ዝግጁነት እንዳነበራቸው ተናግረዋል። ተማሪዎች በጦርነቱ ከደረሰባቸው የስነ ልቦና ጉዳት ሳያገግሙ ፈተና መውሰዳቸው አግባብ አለመሆኑን ተናግረዋል። ዞኑ ለፈተና ከተቀመጡት 9ሺህ 710 ተማሪዎች መካከል የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ያስመዘገቡት 3ሺህ 567 ተማሪዎች ብቻ መሆናቸውን ተናግሯል።

በተጨማሪም ብሔራዊ ፈተና በሰላማዊ መንገድ እንዲሰጥ የሚፈለግብንን ሁሉ አድርገናል ያለው የክልሉ ትምህርት ቢሮ የአንደኛው ዙር ፈተና እንደተጠናቀቀ ለሀገር አቀፍ ፈተናዎች ድርጅት በወቅቱ ፈተና ተሰርቋል እየተባለ በማኅበራዊ ሚዲያ ሲሰራጭ በነበረው የተለያየ መረጃ ምክንያት የፈተና ውጤት ትንተናው በጥንቃቄ እንዲታይ በጽሑፍ ጥያቄ ማቅረቡን  ገልጿል፡፡

ባለፈው ሳምንት የፈተናውን ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ተማሪዎችን እንደገና የመገምገሚያ ጥያቄ እንዲያቀርቡ ሁኔታዎችን አመቻችቷል። በተጨማሪም ቢሮው በትምህርት ሚኒስቴር በውጤት እና በማለፍ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠይቋል።

ተፈራ ፈይሳ ከፈተና እርማት እና ቅሬታዎች ጋር በተያያዘ በሰጡት መግለጫ የፈተናው እርማት ከሰው ንክኪ ነፃ በሆነ መልኩ በጥንቃቄ የተከናወነ ቢሆንም በሁለተኛው ዙር ፈተና እርማት ላይ የቴክኒክ ችግር ማጋጠሙን እና እርማት መደረጉን ገልፀዋል፡፡ በዚህም መሰረት የእርማት ችግሩ የተፈጠረው በ 559 ባልበለጡ ተማሪዎች ላይ እንደሆነ እና ዳግም ምልከታ ተደርጎ ማስተካከያ እንደተደረገም ጨምረው ገልፀዋል፡፡

ዳይሬክተሩ አክለዉም በማህበራዊ ሚዲያ የሚሰራጨው አሉባልታ  ከእውነት የራቀ መሆኑንም ገልፀው ቅሬታዎችን በተመለከተም ተማሪዎች ሳይጉላሉ ባሉበት ቦታ ሆነው ቅሬታቸውን ለመፍታት የሚያስችል ስርዕት ተዘርግቶ  ከ 20ሺህ በላይ ተማሪዎች ቅሬታቸውን አቅርበው ምላሽ መሰጠቱን  ተናግረዋል፡፡ በዘንድሮው አመት የተፈታኝ ተማሪዎች በመብዛታቸው  መግቢያ ነጥብ ከፍ እንደተደረገ ተገልጿል፡፡ በዚህም ምክኒያት ፈተናውን ከወሰዱት ውስጥ 25 ፐርሰንት ተማሪዎች ብቻ ወደ ዩኒቨርስቲ እንደሚገቡ ታውቋል፡፡

ትምህርት ሚኒስቴር በበኩሉ ከ12ኛ ክፍል የመልቀቂያ ውጤት እና ከዩኒቨርሲቲ መግቢያ መቁረጫ ነጥብ ጋር በተያያዘ ተጨማሪ ማብረሪያ ሰጥቷል፡፡

ከትምህርት ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው በ43 የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች በአጠቃላይ 152,144 ተማሪዎች እንዲማሩ የተደረገ ሲሆን ይህም ካለፈው ዓመት በ47 የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች 147,000 ተማሪዎችን ከማስተማር ጋር ሲነፃፀር  ከፍ ያለ መሆኑን አመልክተዋል። ነገር ግን ሚኒስቴሩ የጸጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች የፈተና ውጤትን ለመለየት የግዴታ ምዘና ባለማድረጉ ኤጀንሲው ወጥ የውጤት አሰጣጥ ስርዓትን እንዲያስተናግድ መደረጉን አምኗል።

የብሔራዊ ፈተና ውጤት ውዝግብ ሲከሰት ይህ የመጀመሪያው አይደለም። በ 2011 የትምህርት ሚኒስቴር ባለስልጣናት በሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ላይ አስደንጋጭ የአፈፃፀም ዝቅተኛ ውጤት እና ከተለመደው መደበኛ ስርዓት ውጭ የሆነ አሰራር የተከሰተ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን በወቅቱም  የ12ኛ ክፍል የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና የተፈኑ ከ300,000 በላይ ተማሪዎች ውጤት ከታተመ በኋላ በመላ ሀገሪቱ ቁጣቸውን ለገለፁ ተማሪዎች እና ወላጆች ምላሽ መስጠቱ ይታወሳል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.