ዜና: በኮንሶ ዞን የሰገን ዙሪያ ወረዳ ገቢዎች ፅ/ቤት ኃላፊ ተገደሉ

በጌታሁን ጸጋዬ

አዲስ አበባ መጋቢት 19/2014፡በደቡብ ክልል የኮንሶ ዞን የሰገን ወረዳ የገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ ገረሙ ገለቦ ትናንት ምሽት ከጓደኞቻቸው ጋር በሆቴል ውስጥ እየተመገቡ ሳለ በጥይት መገደላቸው ተገለጸ። ግድያው በተፈፀመበት ምሽት አብረውት የነበሩ ሶስቱ  ጓደኖች እና የሆቴሉ ባለቤት የሆነችው ሴት  በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የወረዳው ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ጋዲሳ ቀሮ ለአዲስ ስታንዳርድ  ተናግረዋል።

ኃላፊው አክለውም ማስረጃዎችን እየሰበሰቡ እንደሆነ ገልጸው “በአካባቢው አንዳንድ የፌደራል ፖሊስ አባላት ነበሩ። ማንነታቸውን እያጣራን እንገኛለን” ብለዋል። ከግድያው ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው ይችላል የሚል ጥርጣሬ እንዳላቸውም ገልጸዋል። ኃላፊው ምርመራው እንደቀጠለ እና ተጨማሪ ሰዎች በቁጥጥር ስር ሊዉሉ  እንደሚችሉም አስረድተዋል።

ጥቃቱ የተፈፀመው እሁድ መጋቢት 18 ቀን 2014 ከምሽቱ 3፡30 ላይ መሆኑን የወረዳው ሰላምና ፀጥታ ቢሮ የገለጸ ሲሆን  ጥቃቱን የፈጸሙት “ቅጥረኛ ሽፍቶች” መሆናቸውን ከመግለጽ ውጪ የወንጀለኞቹን ማንነት  አልተናገረም።  ቢሮው አክሎም ወንጀለኞችን ለህግ እንደሚያቀርብ አስታውቋል።

በኮንሶ ዞን ላለፉት ሁለት አመታት የዘለቀው የድንበር ግጭት እንደቀጠለ በአጎራባች ኮልሜ ክላስተር ቀበሌዎች የሰላም ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ጉዳታ ኩታኖ ለአዲስ ስታንዳርድ ተናግረዋል ።  ግጭቶቹ ለብዙዎች ሞትና መፈናቀል ምክንያት ሆኗልም ብለዋል። አስ  

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.