ዜና: በኢትዮጵያ ጦርነቱ ያደረሰውን ጉዳት እና የሰብአዊ መብት ጥሰት በተመለከተ በጥንቃቄ ምላሽ የሰጡት ብሊንከን በሰላም ስምምነቱ ላይ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል

ፎቶ ከብሊንከን የትዊተር ገጽ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 7/ 2015 ዓ.ም – ትላንት ረቡዕ መጋቢት 6 ቀን 2015 ዓ.ም ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ጥንቃቄ በተሞላበት፣ ላለማስቀየም ጥረት በታከለበት መንገድ በኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አመታት በተካሄደው ጦርነት የተፈጸመውን ግፍ እና ጥፋት አስመልክተው ምላሽ ሰጥተዋል። ትኩረት ማስቀየሻ በሚመስል መልኩ አጽንኦት ሰጥተው ከፕሪቶርያው የሰላም ስምምነት በኋላ ግፉ እና ጥፋቱ መቀነሱ ላይ አተኩረዋል። በተጨማሪም የሰላም ስምምነቱን የፈረሙት ሁለቱም አካላት፣ ፌደራል መንግስቱ እና የህወሓት ሀይሎችየተፈጸመውን ሰብዓዊ መብት ጥሰት እና ያስከተለውን ጉዳት አምነዋል፣ ተቀብለዋል ሲሉ ተደምጠዋል።  

የዛሬ ሁለት አመት በመጋቢት ወር 2021 ላይ በአሜሪካ ኮንግረስ ፊት ቀርበው ምስክርነት የሰጡት ብሊንከን በምዕራብ ትግራይ የተፈፀመው ዘር ያማጽዳት ተግባር ነው ሲሉ ኮንነው ነበር፤ ይህም ጉዳዩን ፊት ለፊት በዚህ መልክ የገለጸ የመጀመሪያው የአሜሪካን መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን ተደርገው ተወስደው ነበር። ይህም አገላለጻቸው በበርካታ አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን እና በሰብአዊ መብት ተቆርቋሪ ተቋማት ማረጋገጫ አግኝቷል።

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በትግራይ የተፈጸመውን ከጦርነት ጋር የተያያዘ ሰብአዊ መብት ጥሰት የዘር ፍጅት ወይንም ጀኖሳይድ መሆኑን የሚያትተውን በ2021 የተደረሰውን ሪፖርት መደርደሪያው ላይ እንዲቀመጥ እና እንዳይቀርብ አድርጎታል ሲል ብሊንከን ወደ አዲስ አበባ ከመምጣታቸው ጥቂት ቀደም ብሎ ፎሬን ፖሊሲ መጽሔት ይፋ አድርጓል። ይህንንም ለጉዳዩ ቅርበት ካላቸው ሶስት ዲፕሎማት መስማቱን መጽሔቱ በዘገባው አስታውቋል።

አዲስ ስታንዳርድ ብሊንከን በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ በነበራቸው ጋዜጣዊ መግለጫ ተገኝቶ ይህንኑ ጉዳይ ጠይቋቸው ነበር፤ ለምን ሪፖርቱ ይፋ አልተደረገም? ሲል።  ጥያቄውን በቀጥታ ከመመለስ ይልቅ በጦርነቱ ወቅት በንጹሃን ላይ የተፈጸሙ ሰብአዊ መብት ጥሰቶች ሀገራችው በተደጋጋሚ በግልጽ ስትኮንን እንደነበር እና በሁሉም ጎራ ያሉ ጥቃቱን የፈጸሙ ተጠያቂ እንዲሆኑ ማቅረቧን አውስተው ይህንን ጉዳይ ከአንድ አመት በፊት እኔ እራሲ ገልጨው ነበር ብለዋል።

ዋናው ትኩረታችን የሚፈጸመው ሰብዓዊ መብት ጥሰት ማስቆሙ ላይ ነው ያሉት ብሊንከን ዛሬም ጭምር በቦታው ከሚገኙ ባለሞያዎች የደረሰን ሪፖርት የሚያመላክተው በትግራይ የሰብአዊ መብት ጥሰቱ በእጅጉን መቀነሱን ነው፤ መቀነሱ እጅግ አስፈላጊ ነው፣ ነገር ግን እንደማንኛውም አከባቢ ዜሮ ደረጃ ላይ ደርሶ መመልከት እንፈልጋለን ብለዋል።

ሌላኛው እና ዋነኛው ጉዳይ የሽግግር ፍትህ ትግበራ ሂደት ቁርጠኝነት ነው፣ ይህም እርቅ ማውረድ እና ተጠያቂነት ያካተተ መሆን አለበት ሲሉ ያሳሰቡት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በዛሬው እለት ካገኘኋቸው ሁሉም አካላት ለመረዳት የቻልኩት ለሂደቱ ቁርጠኛ መሆናቸውን ነው ብለዋል። ይህንንም በሂደት የምናየው ይሆናል ሲሉ የተደመጡት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አንቶኒ ብሊንከን ይህም ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ሀገራት መልካም ቢሆንም ከማንም በላይ ግን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን መሆኑን ገልጸዋል። የተሳካ የሽግግር ፍትህ፣ እርቀሰላም መገንባት፣ ተጠያቂነትን ማስፈን ብቸኛው መንገድ ነው ብሎ መንግስታቸው እንደሚያምን ያስታወቁት ብሊንከን በትግራይ የሰፈነው ሰላም የማይደፈርስ መሆኑን ማረጋገጥ እንደሚፈልጉ አስታውቀዋልን። ሀገሪቱ ወደፊት ልትራመድ የምትችለው ቅሬታዎችን በማስተናገድ፣ ፍትህ በማስፈን፣ ህዝቦችን በማቀራረብ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አንቶኒ ብሊንከን በአዲስ አበባ በነበራቸው ቆይታ ስምምነቱን ከፈረሙት ሁለቱም ወገኖች ተወካዮች ጋር መነጋገራቸውን አስታውቀዋል። ከህወሓት በኩል ተደራዳሪ የነበሩት እና የክልሉ ፕሬዝዳንት አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳን፤ ከፌደራል መንግስቱ በኩል አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር መምከራቸውን አመላክተዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.