ዜና: በአዲስ አበባ የተለያዩ መስጂዶች ሰላማዊ ሰልፍ ተደረገ

ማህሌት ፋሲል

አዲስ አበባ መጋቢት 30/2014 ፣በአዲስ አበባ በሚገኙ የተለያዩ መንግስታዊ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ሰላት በቅጥር ግቢያቸውም ሆነ ከትምህርት ቤት ወጥተው እንዳይሰግዱ በመንግስት አካላት መከልከላቸውን ተከትሎ በዛሬው እለት በመዲናዋ የተለያዩ አካባቢ በሚገኙ የመስጂድ ስፍራዎች ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ።

በወረቀት የተፃፉ መፈክሮችን ይዘው ከወጡት የእስልምና እምነት ተከታዮች መካከል በፖሊስ የታሰሩ እንዳሉ በቦታው ከነበሩት ተማሪዎች ውስጥ አንዱ አብዱል በከር በስልክ  ለአዲስ እስታንዳርድ ተናግሯል :: አብዱ በከር  ከጓደኞቹ  ጋር በታላቁ አንዋር መስጂድ ተገኝተው እንደነበርም ተናግሯል።

“እኛ ጥያቄ ነው ያቀረብነው።  ምንም ነገር አላደረግንም።  መንግስት ከሀይማኖት ላይ እጁን እንዲያነሳ ነው።  በትምህርት ቤት ውስጥም ሆነ ውጪ ሰላት ማድረግ እንደማይቻል ትምህርት ሚኒስቴር ማሳወቁን ተቃውመን ነው።  አሁንም ወደፊትም እንቃወማለን ” ያለ ሲሆን አሁንም መንግስት እጁን ከእምነት ተቋማት ላይ እንዳላነሳ ለአዲስ ስታንዳርድ ያለውን አስተያየት ገልጿል ። አክሎም የጠየቁት ጥያቄ መልስ እስኪያገኝ ድረስ ተቃውሟቸውን እንደማያቆሙ አስረድቷል።  

 አዲስ ስታንዳርድ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ህዝብ ግንኙነት ሀላፊ ኮማንደር ፋሲካ ፈንታ በስልክ ምን ያህል ሰው እንደታሰረና በምን ምክንያት እንደታሰሩ ላቀረብንላቸው ጥያቄ ስብሰባ ላይ እንደነበሩ እና  ምንም መረጃ እንደሌላቸው ተናግረው  መረጃ ካሰባሰቡ በኋላ ሁኔታውን ለማብራራት ፍቃደኝነታቸውን ገልፀዋል።

 አዲስ ስታንዳርድ  በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኙ ሙስሊም ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት የረመዳን ወር መጀመሩን ተከትሎ በርካታ ትምህርት ቤቶች ሰላት እና ሌሎች ተግባራትን በመከልከላቸው ብስጭታቸውንና ቁጭታቸውን እየገለጹ መሆኑን ዘገባ ማውጣቷ ይታወሳል። ሁኔታውን አስመልክቶ የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ የስራ ኃላፊዎች እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ርዕሳነ መምህራን ባደረጉት ውይይት ትምህርት ከሀይማኖታዊ ተግባራት የፀዳ መሆን አለበት ብለው ነበር።

በያዝነው ሳምንት ብዙ ትምህርት ቤቶች ሙስሊም ተማሪዎች በተያዘው የረመዳን ወር የጸሎት ተግባራትን እንዳያከብሩ እና በአንዳንድ አጋጣሚዎች ደግሞ ተማሪዎቹ ከክፍል እንዳይወጡ እየከለከሏቸው እንደሆነ የሚያመላክቱ በርካታ ዘገባዎች ተደምጠዋል ።ታዋቂው የሙስሊም ሊቅ ኡስታዝ አቡበከር አህመድ በሰጡት አስተያየት “ከሰሞኑ በበርካታ ትምህርት ቤቶች ሊያውም በተከበረው በረመዳን ወር የተጀመረው ሰላትን ምክንያት በማድረግ ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታቸው የማራቅ ዘመቻ ከጀርባው ማን እና ምን ይኖር ይሆን የሚለው የሁላችንም ጥያቄ ሆኖ ሰንብቷል።”  በማለት ተናግረዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.