ዜና፡ የጉራጌ ዞን ምክር ቤት በክላስተር ለመደራጀት የቀረበውን የውሳኔ ውድቅ ካደረገ በኋላ የመጀመሪያውን ስብሰባ ነገ ሊያካሂድ ነው

አፈጉባኤ አርሺያ አህመድ። ፎቶ: የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ

በብሩክ አለሙ @Birukalemu21

አዲስ አበባ፣ መስከረም 6/2015 ዓ.ም፡- የጉራጌ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ አርሺያ አህመድ የዞኑ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤውን ነገ መስከረም 07/2015 ዓ.ም. ለማካሄድ ለምክር ቤቱ አባላት ጥሪ መደረጉን ገለፁ

የጉራጌ ዞን ምክር ቤት፤ በነሐሴ ወር መጀመሪያ ላይ ባካሄደው አስቸካይ ጉባኤ ከሌሎች የአስተዳደር መዋቅሮች ጋር በክላስተር ለመደራጀት የቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ በአብላጫ ድምጽ ውድቅ አደርጓል። የጉራጌ ዞንን በደቡብ ክልል ስር ከሚገኙ ሌሎች 4 ዞኖች እና አንድ ልዩ ወረዳ ጋር በማዳመር የጋራ ክልል ለመመስረት የቀረበው የውሳኔ ሀሳብን ከአጠቃላይ 97 የምክር ቤቱ አባላት 52 የምክር ቤት አባላቱ በመቃወም ውድቅ አድርገውታል።

ምክር ቤቱ ከአንድ ወር በፊት ነሐሴ 5፤ 2014 ባካሄደው አስቸኳይ ጉባኤ፤ የጉራጌ ዞንን ከሌሎች የደቡብ ክልል አራት ዞኖች እና አንድ ልዩ ወረዳ ጋር በማዳመር የጋራ ክልል ለመመስረት የቀረበለትን የውሳኔ ሀሳብ በአብላጫ ድምጽ ውድቅ ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን በነገው ስብሰባው ካለፈው ዓመት ዕቅድ፣ አፈጻጸም ግምገማ እና  በጀት ማጽደቅ በዘለለ የክላስተርን ጉዳይ አጀንዳ አይሆንም የሚሉ አባላት አሉ፡፡

ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ያናገራቸው አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የዞኑ የምክር ቤት አባል “የክላስተርን ጉዳይ ሊያመጡት ይችላሉ ብዬ አስባለሁ” ሲሉ ግምታቸውን አስቀምጠዋለል። 

ነገር ግን ዛሬ በውጣው መግለጫ በጉባዔው ላይም የሚነሱ አጀንዳዎች በዝርዝር የተገለፀ ሲሆን የ2014 ዓም የአስተዳደር ምክር ቤት እቅድ አፈጻጸም፣ የዞኑ ፍርድ ቤት የ2014 ዓ.ም ማጠቃለያ ሪፖርት ግምገማ፣ የ2015 የመንግስት የምክርቤቱና የፍርድ ቤት አመታዊ እቅድ እና የ2015 የዞኑ አመታዊ በጀት ላይ በመምከር ዉሳኔ የሚያሳልፍ ይሆነል ነው የተባለው።

ከለይ ከተጠቀሱት አጀንዳዎች ውጪ ሌላ የተለየ አጀንዳ አለመኖሩን እና በጉባኤው መያዝ የሚገባቸው አጀንዳዎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር የተያዙ መሆናቸውን አፈጉባኤዋ በመግለጫቸው ገልጸዋል። ጉባኤው የሚመራው በህገመንግስቱ መነሻነት ከፌደራልና ከክልል ህገመንግስት መነሻ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምክርቤት በተዘጋጀው የአሰራር ስነምግባር መሰረት ይመራል።

በመሆኑም ጉባኤው ፍጹም ሰላማዊ፣ ያማረና የዞኑ ማህበረሰብ የሚመጥን እንዲሆን የተዘጋጀ መሆኑን ዋና አፈጉባኤዋ ገልጸዋል። የዞኑ ማህበረሰብ በሀገሪቱ ህልውና ላይ የማይደራደር፣ ለሀገር ክብርና ሰላም ደጀንነቱን በተግባር ያረጋገጠ ህዝብ ነው ያሉት አፈጉባኤዋ በጉባኤው የሚቀመጡ አቅጣጫዎች ተከትሎ የልማት እና የአካባቢውን ሰላም የማስጠበቅ ስራው አጠናክሮ መቀጠል አለበት ሲሉም አሳስበዋል።

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የወላይታ፣ የጋሞ፣ የጎፋ፣ የደቡብ ኦሞ፣ የጌዴኦ፣ የኮንሶ ዞኖች፣ እንዲሁም የደራሼ፣ የአማሮ፣ የቡርጂ፣ የአሌ እና የባስኬቶ ልዩ ወረዳ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በጋራ ”የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል” የመመስረት ጥያቄ ከሕገ መንግሥቱ አንፃር ውሳኔ ለመስጠት እንዲያስችል የሕዝብን ይሁንታ ማረጋገጥ ስለሚያስፈልግ ከማንኛውም ተጽእኖ ነጻ በሆነ መልኩ ገለልተኛ በሆነው ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አማካኝነት በሦስት ወር ጊዜ ውስጥ ሕዝበ ውሳኔ እንዲደራጅና የሕዝብ ውሳኔው ውጤት ሪፖርት ለምክር ቤት እንዲቀርብ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

ነሐሴ 12 ቀን 2014 ዓ.ም የፌዴሬሽን ምክር ቤት ባደረገው ስብሰባ በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል የሚገኙ የ6 ዞኖች (የጋሞ፣ ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴኦ፣ ኮንሶ እና የደቡብ ኦሞ ዞኖች) እና የ5 ልዩ ወረዳዎች(የቡርጂ፣ የአማሮ፣ የደራሼ፣ የባስኬቶ እና የአሌ ) በአንድ ክልል የእንደራጅ አቤቱታን ተቀብሎ ከመረመረ በኃላ በብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አማካኝነት ሕዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ ውሳኔ ማስተላለፉ  ይታወሳል፡፡

ጉራጌ ዞንን ጨምሮ ሀድያ፣ ሀላባ፣ ከምባታና ጠምባሮ፣ ስልጤ እና የም ልዩ ወረዳ በነባሩ የደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል አንድ ላይ አንድ ላይ እንዲቀጥሉ ውሳኔ አስተላልፏል። 

የጉራጌ ዞን በደቡብ ክልል ከሚገኙ መዋቅሮች ውስጥ የ“ክላስተር” አደረጃጀትን ባለማጽደቅ ብቸኛው ነው። 

የክላስተር የመደራጀት ውሳኔውን በመቃወመም በወልቂጤ ከተማ ሁለት ጊዜ ስራ የማቆም አድማ ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ በተጨማሪም የዞን የክላስተር አደረጃጀትን የሚቃወሙ በርካት የዞኑ አመራሮች እና  የመምሪያ ኃላፊዎች መታሰራቸው የሚዘነጋ አይደለም፡፡

ይህንን ተከትሎ ነሐሴ 18 ቀን የክልሉ ኮማንድ ፖስት ለሁለተኛ ጊዜ ባወጣው መግለጫ በከተማው የንግድ ሱቆችና የንግድ ድርጅቶች ያለምንም ምክንያት መዝጋትና በከተማው በቀን 19/12/2014 ዓ.ም ጀምሮ ባንኮች፣ የተለያዩ የመንግስትና የግል ተቋማት መዝጋት እነደማይቻል እንዲሁም የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሬዎች ስራ ማቋረጥ በጥብቅ የተከለከለ መሆኑን ገልፆ ይህን ትእዛዝ በሚተላለፉ አካላት ላይ በዞኑ የተቋቋመው ጊዜያዊ ኮማንድ ፖሰቱ እርምጃ እንደሚወስድ ቢያሳስብም ህብረተሰቡ ግን የራሱን እርምጃ ከመተግበር ወደ ኋላ ሳይል የሁለት ቀን ስራ የማቆም አድማ አድርጓል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.