ዜና፡ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በትግራይ በርካታ ቅርንጫፎቹ የተሟላ የባንክ አገልግሎት ጀመረ፤ በየትኛውም የሃገሪቱ ክፍል የተከፈቱ የሂሳብ ደብተሮች መጠቀም ይቻላል ተባለ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 2/ 2015 ዓ.ም፡- የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በትግራይ ክልል በሽሬ፤ አክሱም፤ ዓድዋ፤ ሰለኽለኻ፤ ማይ ፀብሪ፤ እንዳባጉና፤ ውቕሮማራይ፤ ዓዲግራት፣ ውቕሮ፣ ፍረወይኒ፣ ሓውዜን፣ ዓዲጉዶም፣ ሒዋነ፣ ዓዲሽሁ፣ መኾኒ፣ ማይጨውና አካባቢው በሚገኙ በርካታ ቅርንጫፎች የተሟላ የባንክ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን አስታወቀ፡፡

ባንኩ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት እደገለጸው፥ አገልግሎት መስጠት በጀመረባቸው ቅርንጫፎች ለደንበኞች የተሟላ የባንክ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ “የባንኩ ደንበኛ የሆነ ማንኛውም ሰው በየትኛውም የሃገሪቱ ክፍል የከፈተውን የሂሳብ ደብተር ይዞ በመቅረብ አገልግሎት ማግኘት ይችላል” ሲልም ጨምሮ ገልጿል፡፡

በተለያየ ምክንያት የሂሳብ ደብተራቸው የጠፋባቸው ደንበኞች ካሉ መታወቂያቸውን ይዘው በመቅረብ ባንኩ ከዚህ ቀደም ይጠቀምበት በነበረ አሰራር መሰረት የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን እንደሚችሉ ባንኩ ከመቐለ ዲስትሪክት ያገኘውን መረጃ አጣቅሶ ገልጿል፡፡

“የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በመቐለ ከተማ በሚገኙት ሁሉም ቅርንጫፎች እንዲሁም በዓብይ ዓዲ፤ ማይ ለሚን፤ ሳምረ፤ ግጀት፤ ሃይቂ መስሓል፤ወርቅ አምባ፤ አፅቢ እና አጉላዕ እና በሌሎች አካባቢዎች በሚገኙ በርካታ ቅርንጫፎች በትናንትናው ዕለት የተሟላ የባንክ አገልግሎት መስጠት” መጀመሩምን አያይዞ ገልጿል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.