ዜና፡ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንትን ጨምሮ አራት የዩኒቨርሲቲ መምህራን ከስራ ማቆም አድማ ጋር በተያያዘ ታሰሩ

አዲስ አበባ፣ ህዳር 27/ 2015 ዓ.ም፡- ከትናንት ጀምሮ በተለያዩ የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች እየተካሄደ ካለው የስራ ማቆም አድማ ጋር በተያያዘ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንትን ጨምሮ አራት መምህራን መታሰራቸው የዩኒቨርስቲው መምህራን ገለፁ፡፡

ስሟ እንዲጠቀስ ያልፈለገች የዩኒቨርሲቲው መምህርት ለአዲስ ስታንዳርድ እንደገለፀችው ስራ የማቆም አድማውን አስተባብራችኋል በሚል የአርባ ምንጫ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ማህበር ፕረዘዳንት ምክትል ፕረዝዳንቱን እና ሌሎች ሁለት መምህራን እንደታሰር ገልፃ ሆኖም ግን  ፕረዘዳንት መፈታታቸውን አስርዳታለች፡፡

ቀሪዎቹ መምህራን እስካሁን አለመፈታታቸውን የገለፀችው መምህሯ የመማር ማስተማር ሂተዱ ከትላንት ጀምሮ መቋረጡንና  ሁሉም መምህራኑ አንድ ላይ ተሰባስበው ወደ ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ የታሰሩት መምህራን እንዲፈቱ ጥያቄ አቅርበዋል ብላለች፡፡

የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ መመህራን የስራ ማቆም አድማውን በመቀላቀል ትላትና እና ዛሬ ስራ አለመግባታቸውን የዩኒቨርሲቲው መመህራን ማህበር ፕረዜዳንት ፍቅረስላሴ አካሉ ገልፀዋል፡፡ ፕረዜዳንቱ “ስራ የማቆም አድማው ጥያቆዎቻችን እስኪመለሱ ድረስ የሚቀጥል ይሆናል” ሲሉ ለአዲስ ስታንዳርድ ተናግረዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ በርካታ ዩኒቨርሲቲዎች አድማውን አጠናክረው ቀጠለዋል ያሉ ሲሆን በትላንትናው እለት አድማውን ያላደረጉ ዩኒቨርሲቲዎች በዛሬው እለት መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ጥያቄውን ማንሳት የነበረበት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ቢሆንም ለፖለቲካው ባለው ውግንና መምህራን እንዲቸገሩና እዚህ ደረጃ ላይ እንዲደርስ አድርጓል ይላሉ፡፡

ማህበሩ ህጋዊ እውቅና ያለው መሆኑን ገልፀው ማህበሩ ስብሰባ ጠርቶ ስራ የማቆም አድማው ላይ ውይይት በማድረግ እንዳለ የማህበሩ ሃላፊዎች  በፖሊስ መታሰራቸውን ፍቅረስላሴ ተናግረዋል፡፡

በወለዲያ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑ የመረጃ ምንጫችን በበኩላቸው ከትላንት ጀምሮ የመማር ማስተማሩ ሂደት ቆሟል፡፡ “በወር ከሚያገኘው 8000 ሺ ደመመዝ እስከ 6000 ብሩን ለቤት ክራይ ብቻ እየከፈል ቤተሰቡን ማስተዳደር የተሳነው መምህር ስራ የማቆም አድማ ከማድረግ ውጭ ሌላ አማራጭ የለውም” ብለዋል፡፡

የመምህራን ጥያቄ የፖለቲካ ጥያቄ አይደለም የሚሉት መምህሩ ጉዳዩ የመኖርና ያለመኖር በመሆኑ መንግስት ጥያቄዎቻችንን መመለስ አለበት ብለዋል፡፡ መምህሩ አያይዘውም በግቢው ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎችን ሌሎች አገልግሎቶችን እያገኙ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲዎች መምህራን እና ቴክኒካል ረዳቶች ለትምህርት ሚንስቴር እና ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በፃፉት ደብዳቤ መሰረት ከህዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ላልተወሰነ ጌዜ የስራ ማቆም አድማ እንሚያደርጉ ማስታወቃቸው ይታወሳል፡፡ አዲስ ስታንዳርድ በጉዳዩ ላይ ያነጋገራቸዉ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ጥያቄያቸው ስላልተመለሰላቸው ወደዚህ ዓይነት ውሳኔ እንደደረሱ ይናገራሉ፡፡

መምህራኑ በፃፉት ደብዳቤ እንዳሰፈሩት የመነሻ ደመወዝ ማነስ፣ የአገልግሎት ጭማሪ አለመደረግ፣ ወቅቱን የሚመጥን ከታክስ ነጻ የሆነ የቤት ኪራይ አለማግኘት፣ የሶስተኛ ዲግሪ የምርምር ገንዘብ መጠን በቂ አለመሆን፣  የትርፍ ሰዓት ክፍያዎች አለመስተካከል እና  የደረጃ ዕድገት መቋረጥ በሚመለከት እንዲሻሻል ጠይቀዋል። የስራ ማቆም አድማው የሚካሄደው ላልተወሰነ ጊዜ መሆኑንም በደብዳቤው ማስፈራቸው ይታወሳል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.