ዜና፡ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሁሉም የወርቅ አምራች ኩባንያዎች ምርቶቻቸውን ለብሄራዊ ባንክ እንዲሸጡ መመሪያ አስተላለፈ


አዲስ አበባ፣ ህዳር 12/ 2015 ዓ.ም፡- በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚንቀሳቀሱ ሁሉም የወርቅ አምራች ኩባንያዎች፣ አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች እና ማህበራት የወርቅ ምርቶቻቸውን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እንዲሸጡ መመሪያ አስተላለፈ።

የክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ አሻድሊ ሀሰን ማንኛውም ድርጅት በክልሉ ውስጥ እያመረቱት ያለ የወርቅ ምርት ለብሔራዊ ባንክ ማስረከብ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ ፕሬዝዳንቱ በአሶሳ ዞን ዳቡስ ወረዳ በጥቃቅን ልዩ ኢንተርፕራይዞች ከሚተዳደሩትን የወርቅ ማምረቻ ቦታዎች አንዱን መጎብኘታቸውን የክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮዘግቧል።

ወርቅን በህገ ወጥ መንገድ ሲያዘዋውሩ የነበሩ አካላት ወርቅ ወደ  ብሄራዊ ባንክ እንዳይገባ የማድረግ አላማ ብቻ ሳይሆን ያነገቡት በሀገሪቱ ኢኮኖሚ መረጋጋት እንዳይፈጠር ለማድረግ ጭምር መሆኑን ፕሬዝዳንቱ ተናግረዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተለያዩ ኩባንያዎችና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች የሚመረተው ወርቅ ሙሉ በሙሉ ወደ ብሔራዊ ባንክ እየገባ እንዳልሆነም ፕሬዝዳንቱ አስታውቀዋል።

ፕሬዝዳንቱ አያይዘውም የወርቅ ምርትን በሚደብቁ አምራቾች እና በህገ ወጥ መንገድ በዝውውር በሚሰማሩ ግለሰቦች ላይ እየተወሰደ ያለው  እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።

የሚያመርቱትን ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ የሚያቀርቡ ኩባንያዎችና ልዩ አነስተኛ ድርጅቶች የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግላቸውም ጠቁመዋል። በብሄራዊ ባንክ ለወርቅ አቅራቢዎች ማበረታቻ ክፍያ ከ29 በመቶ ወደ 35 በመቶ  ከፍ ብሏል፣ ይህም ለአምራቾች፣ ለዕደ-ጥበብ አምራቾች የሚያግዝ ሲሆን  ሕገወጥ የወርቅ ኤክስፖርትን ለማስወገድ ታስቦ የተደረገ እንደሆነም  ተናግረዋል።

ክፍያውን ለማሳደግ የታሰበው በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ “መመሪያ” ከቀረበ በኋላ ሆኖ የማዕድን ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ጥምር ኮሚቴ መወሰኑም ይታወቃል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.