ዜና፡ የራያ ቆቦ ኮሙኑኬሽን በኮምቦልቻ የሚገኙ የራያ ተፈናቃዮች ድብደባና እስር እየተፈፀመባቸው መሆኑን ገለፀ ፤ የኮምቦልቻ ኮምዩኒኬሽን መረጃው ሀሰትና መሰረተ ቢስ ነው ሲል አስተባበለ

የኮምቦልቻ ከተማ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 4/2014 ዓ.ም፡- በጦርነቱ ምክንያት ተፈናቅለው በደቡብ ወሎ ዞን ኮምቦልቻ ከተማ የሚገኙ የራያ ተፈናቃዮች በፀጥታ ሀይሎች ድብደባ፣ማሸማቀቅና እስር እየተፈፀመባቸው መሆኑን ገልፀዋል ሲል የራያ ቆቦ ኮሙኑኬሽን አስታወቀ፡፡ የኮምቦልቻ ኮምዩኒኬሽን በበኩሉ መረጃው “ሀሰትና መሰረተ ቢስ” መሆኑን የሰላምና ደህንነት መምሪያ ገለጿል ሲል አስታውቋል፡፡

የራያ ቆቦ ኮሙኑኬሽን ጽ/ቤቱ  በፌስ ቡክ ገፁ  “ኮምቦልቻ ከተማ የሚገኝ የራያ ተፈናቃይ ዜጋ አይደለም ወይ ? የወሎን መልካም ስም ለማጠልሽት እስከሚመስል ድረስ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት እየተፈፀመብን ነው” ሲሉ የድብደባው ሰለባ የሆኑ ተፈናቃዮች መናገራቸውን ገልጧል፡፡ አክሎም ከኮምቦልቻ ከተማ ሰላምና ደህንነት ፅ/ቤት ሀላፊ አቶ ሙህየ ይማምን በጉዳዩ ዙሪያ ለማነጋገር የደረገው ጥረት አልመሳካቱን አሳውቋል፡፡

ይህንን ተከትሎ ኮምቦልቻ ኮምዩኒኬሽን ባወጣው መግለጨጫ የራያ ቆቦ ኮሙኑኬሽን በፌስ ቡክ ገጹ “በኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር የራያ ተወላጆች እስርና እንግልት ደረሰባቸው” ብሎ የለቀቀው መረጃ ሀሰትና መሰረተ ቢስ መሆኑን የሰላምና ደህንነት መምሪያ መግለፁን አስታውቋል።

የሰላምና ደህንነት መምሪያው ኃላፊ አቶ ሙህዩ ይማም ለመንግስት ኮምዩኒኬሽን ጽ/ቤት በሰጡት አስተያየት የህወሃት ቡድን ያቀደው ዕቅድ አልሳካ ሲለው በማወቅም ይሁን ባለ ማወቅ ከግለሰብ እስከ ታዋቂ ገጾች በከተማችን ላይ ያልተገባ የገጽታ ማጥፍት ስራ እያካሄደ መሆኑን ስለደረስንበት ባለማወቅ እንደዚህ አይነት መረጃ የምትለጥፉ ወገኖች የቡድኑ ዕቅድ መሆኑን አውቃችሁ ከዚህ ድርጊታችሁ እንድትቆጠቡ እናሳስባለን ብለዋል።

የኮምቦልቻ ማህበረሰብ ህወሃት  ለሚፋለመው ጥምር ጦር ደጀን በመሆን እስከ ምሽግ ገብቶ ስንቅ የሚያቀብል፣ በህወሃት ምክኒያት የተፈናቀሉ ወገኖች በወሎየነት የእንግዳ አቀባበል ባህልና ወግ ካለው ላይ ላንተ ብሎ የሚያጎርስ አሁንም ያንን እያደረገ ያለ ማህበረሰብ መሆኑን መታወቅ እንዳለበትም አሳስበዋል።

ኃላፊው የህውሃት ቡድን በከተማው ውስጥ አሉባልታ በማውራት ማህበረሰብን በማሸበር ለዘረፍና በልዩ ልዩ የውብድና ወንጀል ለመሳተፍ አስርጎ ያስገባቸው ጸጉረ ልውጥ ሰዎች መያዛቸውን አክለው ገልጸዋል።

“በቡድኑ በወረራ የተያዙ አካባቢ ነዋሪዎች እንግዶቻችን ናቸው” ያሉት ኃላፊው ይህን  ቡድን አብረን ታግለን ሰጋት በማይሆንበት ደረጃ አድረሰነዋል ወደፊትም አብረን እናታገለዋለን ሲሉም ተናግረዋል።

የጸጥታ ተቋማችንም በአስተማማኝ ቁመና ላይ የሚገኝ ሲሆን ለወንጀል ለዘረፍ የሽብር ተግባር ለመፈጸም ያቀደ ካለ ከህዝቡ ጋር በመሆን ወደፈትም ተጠያቂ እንዲሚሆን  አሳስበዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.