ዜና፡ የምስራቅ አፍሪካ ወታደራዊ ተቋማት በጋራ ለመስራት ተስማሙ፣ የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ የፓትሮል ቅኝት ተግባራትን ለማጠናከር እንደሚሰራ አስታወቀ

ጌታሁን ፀጋዬ

ሚያዚያ 10፣ 2014፣ አዲስ አበባ –የምስራቅ አፍሪካ ወታደራዊ መረጃ ተቋማት ከሚያዚያ 8 እስከ 9፣ 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በተደረገው የጋራ የውይይት መድረክ ላይ በቀጠናው ፀጥታና ደህንነት ጉዳዮች ዙርያ  በጋራ ለመስራት መስማማታቸውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አስታወቀ

በምክክር መድረኩ የተሳተፉ ሀገራት ጁቡቲ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን፣ ታንዚያና፣ ኡጋንዳ እና ኢትዮጵያ ሲሆኑ  “ሠላማዊ እና ደህንነቷ የተረጋገጠ አፍሪካን ” ለመፍጠር በሚል በሪ ቃል  በድንበር፣ በሳይበር፣ በማህበራዊ ሚዲያ ዙርያ፣ በማህበራዊ ጉዳዮች፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በወጣቶችና ሥራ አጥነት በሌሎችም ጉዳዮች ለመሥራት የተስማሙ ሲሆን አሸባሪዎችንና ፀረ ሠላም ኃይሎችን በጋራ ለመከላከል የሚያስችል ሰነድም ተፈራርመዋል።

በመድረኩ ከጸጥታ ጉዳዮች በተጨማሪ የልምድ ልውውጥ አጀንዳዎችን ያካተተ ሲሆን ተሳታፊዎቹ የኢትዮጵያ ብሔራዊ መከላከያ ዋና መስሪያ ቤት፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ቢሮ እና የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን ጎብኝተዋል። ዩጋንዳ ቀጣዩን መድረክ እንደምታዘጋጅ ተነግሯል።

የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ በበኩሉ የህብረተሰቡን የጸጥታ ጥበቃን በማጠናከር ወንጀልን ለመከላከል በቅንጅት እየሰራ መሆኑን አስታውቋል። የአዲስ አበባ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር የሰላምና እሴት መምሪያ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ሊዲያ ግርማ እንደተናገሩት ቢሮው ከህብረተሰቡ ጋር በመተባበር በከተማዋ የሚስተዋሉ ህገወጥ ድርጊቶችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር እየሰራ ነው።

.ከዚህ በፊት የነበረውን ይህንን ህዝባዊ ሰራዊት ከማዕከል እስከ ወረዳ በብሎክ እንደገና በማደራጀት ህዝባዊ መሠረት እንዲኖረው በማድረግና ወደ ስራ ለማስገባት እየሰሩ መሆኑንም  ተናግረዋል። ምክትል ኃላፊዋ አክለውም  ህዝቡ ከፀጥታ ሃይሉ እና ከሰላም አካላት ጋር በመተባበር ህገወጥ ድርጊቶችን በሚመለከት መረጃ በመስጠት ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

የማህበረሰቡን የፀጥታ የፓትሮል ቅኝት ተግባራትን በማጠናከር ወንጀልን በጋራ ለመከላከል  ከሚያዚያ 10 ጀምሮ ከ30 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሲቪል  የማህበረሰብ የፀጥታ አካላት በወንጀል መከላከል እና በመልካም ስነ ምግባር ዙርያ ላይ በሁሉም ክፍለ ከተሞች የአቅም ግንባታ ስልጠና እንደሚሰጣቸውም ተገልጿል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.