ዜና፡ እንግሊዝ በድርቅና በግጭት ለተጎዱ ኢትዮጵያውያን 16.6 ሚሊዮን ፓውንድ ድጋፍ አደረገች፤ የአለም አቀፉ ማህበረሰብ  “በኢትዮጵያ እየተባባሰ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስ” እንዳይዘነጋ ጥሪ አቀረበች

ፎቶ ዩኒሴፍ/ክሪሰቲን ኔሰቢት

አዲስአበባ፣ ጥር፣13/ 2015 ዓ.ም፡- ኢንግሊዝ በኢትዮጵያ ውስጥ  የጸጥታ ችግር እየተባባሰ በመጣባቸው አካባቢዎች የሚገኙ ከ600,000 በላይ ለሚሆኑ ኢትዮጵያውያን የሚውል የ16.6 ሚሊዮን ፓውንድ ድጋፍ ማድረጓን  የእንግሊዝ የልማት ሚኒስትር አንድሪው  ሚካኤል ገልፁ፡፡ በተጨማሪም የአለም አቀፉ ማህበረሰብ  “በኢትዮጵያ እየተባባሰ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስ” እንዳይዘነጋ ኢንግሊዝ ጥሪ አቅርባለች፡፡

የ11.6 ሚሊዮን ፓውንድ ድጋፉ የሚውለው ለሴፍቲ ኔት ፕሮግራም (PSNP) እነዲሁም “በመላው ኢትዮጵያ በከፍተኛ የስብእዊ ቀውስ ውስጥ ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ዜጎች የሚውል ሲሆን ይህም ኦሮሚያ፣ ትግራይ፣ አማራ እና አፋር እና ሀረሪ ክልሎች በድህነት ውስጥ ለሚገኙ ወደ 250,000 የሚሆኑ ዜጎችን ይውላል” ተብሏል።

ቀሪው 5 ሚሊዮን ፓውንድ በአለም ምግብ ፕሮግራም (WFP) በኩል በተመጣጠነ ምግብ እጥረ ለሚቸገሩ ወደ 23,000 ለሚጠጉ ነፍሰ ጡር እና ለሚያጠቡ ሴቶች  የሚውል ሲሆን  በ75 ትምህርት ቤቶች ለ 42,000 ተማሪዎች የተሻለ የምገባ መርሃ ግብሮችን ለማቅረብ የሚውል መሆኑን ድጋፉን ይፋ ያደረገው  መግለጫ አስታውቋል። 

“ድጋፉ የተበረከተው በመላው ኢትዮጵያ ወደ 30 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች በከባድ ችግር ውስት ባሉበት ወቅት  ነው፤ ይህ የህይወት አድን ድጋፍ በሺዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ተደራሽ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውስጥም ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ሴቶች እና ህፃናት ሲሆኑ እየተባባሰ ባለው  የሃገሪቷን ችግር የተሸከሙ ናቸው” ሲሉ አንድሪው ተናግረዋል፡፡

በሰሜናዊ እና ምዕራባዊ ክልሎች ብቻ “22 ሚሊዮን ሰዎች በድርቅ፣ በግጭት እና በኢኮኖሚያዊ ጫናዎች ምክንያት አስከፊ የምግብ ዋስትና እጦት እያጋጠማቸው ነው” ስትል እንግሊዝ ገልጻለች፡፡  “በትግራይ ውስጥ በህዳር ወር የሰላም ስምምነት ከተፈረመ በኋላ የሰብአዊ ድጋፍ አቅርቦት የተሻሻለ ቢሆንም  እጅግ በጣም ብዙ ሰዎች አሁንም የምግብ፣ ነዳጅ እና የጤና እንክብካቤን ጨምሮ አስፈላጊ አቅርቦቶችን እና መሰረታዊ አገልግሎቶችን የማግኘት ውስንነት አለ” ብለዋል። 

የኦሮሚያ ክልልን ጨምሮ በሌሎች አካባቢዎች ግጭቶችና እና የጸጥታ ችግር መባባሱ ቀጥሏል። “የፀጥታ ችግር ሁኔታ እየተባባሰ በመምጣቱ ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ሰላማዊ ዜጎች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል፣ በርካቶች የእርዳታ ድርጅቶች ሊደርሱባቸው በማይችሉበት ሁኔታ፣ እንደ ኤሌክትሪክ፣ የሞባይል ኔትወርክ፣ የጤና ተቋማት እና ባንኮች ያሉ አስፈላጊ አገልግሎቶችን ማግኘት አልቻሉም” ሲል ገልጧል መግለጫው፡፡

እንግሊዝ ለኢትዮጵያ ያበረከተችው የገንዘብ ድጋፍ በዚህ ዓመት የተበረከተውን አጠቃላይ የሰብአዊ ድጋፍ ወደ 49.2 ሚሊዮን ፓውንድ እንዳደረሰው በመግለጫው ገልጾ ባለፉት 17 ዓመታት እንግሊዝ ለሴፍቲ ኔት ፕሮግራም ብቻ 650 ሚሊዮን ፓውንድ ሰጥታለች ብሏል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.