ዜና፡ አሜሪካ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በትግራይ የእርዳታ አቅርቦታቸውን ማቋረጣቸውን አስታወቁ

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 26/2015 ዓ.ም፡- የአሜሪካን መንግስት የእርዳት አቅርቦት ድርጅት ዩኤስኤድ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብ ፕሮግራም በትግራይ የሚያካሂድቱን የእርዳት አቅርቦት ለጊዜው ማቋረጣቸውን አስታወቁ።

የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤይድ አስቸጋሪ ውሳኔ ቢሆንም በትግራይ የምናደርገውን የእርዳታ አቅርቦት ለማቋረጥ ተገደናል ሲሉ ዋና ሃላፊዋ ሳማንታ ፓወር መናገራቸውን በድረገጹ አስነብቧል። ሳማንታ ፓወር በመግለጫቸው በትግራይ ለተቸገሩ ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ በሚል የቀረበው እህል በአከባቢው ገበያዎች ለሽያጭ መቅረቡን አስታውቀው ተቀባይነት የሌለው ተግባር ሲሉ ኮንነዋል። ድርጅታቸው ጉዳዩን እያጣራው መሆኑን አመላክተው፤ ጉዳዩን እንዲመረምር ከዋናው የኢትዮጵያ ቢሮ ከፍተኛ ባለሞያዎች መላካቻውንም ጠቁመዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ ከፌደራል መንግስቱ እና ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር መምከራቸውንም ሳማንታፓወር አስታውቀዋል። ሁለቱም አካላት ከዩኤስኤይድ ጋር በመተባበር ተጠያቂዎችን ለመለየት እና ለፍርድ ለማቅረብ ፈቃደኛ መሆናቸውንም ገልጸውልናል ብለዋል። ጉዳዩ እልባት እንዳገኘ ዩኤስኤይድ በማንኛውም ሰዓት እርዳታውን ለማስጀመር ዝግጁ መሆኑንም በመግለጫው አስታውቋል።

የአለም የምግብ ፕሮግራም በበኩሉ ትላንት በድረገጹ ይፋ ባረደገው መግለጫ እንዳስታወቀው በትግራይ ለተጎጂዎች ይደርሳል ተብሎ የተከማቸ እህል ለሌላ አላማ መዋሉ እጅግ እንዳሳሰበው ገልጿል። ጉዳዩን በአጽንኦት እንደሚከታተለው ያሳሰበው የአለም የምግብ ፕሮግራም ለተጎጂዎች የምግብ እርዳታ ተደራሽ ለማድረግ በሚያደርገው ጥረት ጣልቃ ለሚገባ ሁሉም አካል ምንም አይነት ትግስት እንደማይኖረው ገልጿል። በትግራይ በሚያካሂደው የእርዳታ አቅርቦት ችግር መፈጠሩን እንዳወቀ ወዲያውኑ የተሟላ ምርመራ ማስጀመሩን ያመለከተው መግለጫው የእርዳታ አቅርቦት እንዲቋረጥ ማድረጉን እና ሁኔታው ተጣርቶ እርዳታው ለታለመለት አላማ እንደሚውል እስኪያረጋግጥ ድርስ እንደማይቀጥል አመላክቷል።

በጉዳዩ ዙሪያ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳን አቶ ጌታቸው ረዳ በማህበራዊ ሚዲያ የትዊተር ትስስር ገጻቸው በሰጡት ማብራሪያ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት በጉዳዩ ዙሪያ ከተለያዩ አካላት በእርዳታ እቅርቦቱ ላይ የተፈጠረውን ችግር የተመለከቱ መረጃዎች እንደደረሳቸው አስታውቀው ጉዳዩ እጅግ አሳሳቢ በሆኑ እና በቀረበው ማስረጃ መሰረት ከፍተኛ መርማሪ ቡድን ተሰይሟል ብለዋል። ምንም አይነት የሀላፊነት እና ዳራ ያለው ሰው ይሁን ተጠያቂ ይደረጋል ሲሉ የገለጹት አቶ ጌታቸው ረዳ የእርዳታ አቅርቦት ተቋማት ስራቸውን እንዲቀጥሉ ተማጽነዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.