ዜና፡- ንግድ ባንክ በጦርነቱ ምክንያት አገልግሎት አቋርጠዉ የነበሩ ሰባት ቅርንጫፎች ስራ መጀመራቸውን ገለፀ

አዲስ አበባ፣ህዳር 3/2014 ዓ.ም፡- በትግራይ ክልል ተከስቶ በነበረው ጦርነት ምክንያት አገልግሎት ተቋርጦባቸዉ የነበሩ በሽሬ ዲስትሪክት ስር የነበሩ እና በምእራብ ትግራይ የሚገኙ ሰባት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፎች ማለትም የማይካድራ፣ ሁመራ፣ ቃፍታ ፣ አውሮራ፣ ዳንሻ፣ አዲ ረሚፅ እና ከተማ ንጉስ ቅርንጫፎች ስራ መጀመራቸውን ባንኩ አስታወቀ።

እነዚህ ሰባቱ የባንኩ ቅርንጫፎች ለጊዜው በጎንደር ዲስትሪክት ስር ታቅፈው አገልግሎት እንዲጀምሩ መደረጉን የባንኩ ኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አልሰን አሰፋ ለአዲስ ስታንዳርድ ተናግረዋል።

አክለዉም ሌሎች እንደ ማይጸብሪ፣ አይካል እና አዲሄርዲ፡ ተከዜ፣ አዲ ጎሹ፣ ቆራሪት፣ ማይጋባ፣ ሰቲት እና አደባይ ቅርንጫፎች በቅርቡ ወደስራ የሚገቡ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በትግራይ ክልል ሁላት ዲስትሪክቶች ያሉት ሲሆን በሽሬ ዲስትሪክት 59 ቅርንጫፎች በመቀሌ ዲስትሪክት ደግሞ 61 ቅርንጫፎች አሉት።

በመቀሌ ዲስትሪክት ስር ካሉት 61 ቅርንጫፎች ውስጥ ሰባቱ ማለትም ኮረም፣ ሃሸንጊ፣ አላማጣ፣ ራያ፣ አንሳር፣ ጁሃን፣ ዋጃና ጥሙጋ በወልዲያ ዲስትሪክት ስር ታቅፈው ስራ እንዲጀምሩ እየተሰራ መሆኑንም አቶ አልሰን ተናግረዋል።

በጦርነቱ ምክንያት ተዘግተዉ የቆዩ ሌሎች የባንኩ ቅርንጫፎችም እንደ ሁኔታዎች ምቹነት ወደ አገልግሎት ለመመለስ እየተሰራ ነዉም ብለዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት እና የትግራይ አመራሮች ግጭት ለማቆም የጋራ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተከትሎ መንግስት ቃል የገባዉን ያልተገደበ የሰበአዊ እርዳታ እና መሰረታዊ አገልግሎቶች ዳግም እንዲጀምር የአለም አቀፉ ማህበረሰቡ ጥሪ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡

ይህን ተከትሎም በትግራይ ክልል አገልግሎቶች ዳግም እየጀመሩ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደህንነት አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ገልፀዋል። ክልሉ 70 በመቶ በመከላከያ ሰራዊት ቁጥጥር ስር መሆኑን የገለፁት አምባሳደር ሬድዋን ዕርዳታው ከመቼውም ጊዜ በላይ ወደክልሉ እየገባ መሆኑንም ጠቁመዋል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.