ዜና፡ በየቀኑ ከአንድ ሺ በላይ የሱዳን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ አለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አስታወቀ

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 28/2015 ዓ.ም፡- በጎረቤት ሱዳን በተፈጠረው ቀውስ ሳቢያ በየቀኑ ከአንድ ሺ በላይ ስደተኞች የኢትዮጵያን ድንበር አቋርጠው እንደሚገቡ አለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) አስታወቀ። የሱዳን ግጭት ከተጀመረ ወዲህ በመተማ በኩል ወደ ኢትዮጵያ የገቡ የሱዳን ስደተኞች ቁጥር ከ12 ሺ በላይ መድረሱን ያስታወቀው ድርጅቱ ስደተኞቹም ሱዳናውያን፣ በስደት በሱዳን ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን እና የሌሎች የሶስተኛ ሀገራት ዜጎች መሆናቸውን ጠቁሟል።

አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) የኢትዮጵያን ድንበር አቋርጠው የሚገቡ ስደተኞችን በማገዝ ላይ መሆኑን አመላክቶ የሚሰጣቸው እገዛወችም ከድንበር አከባቢ ወደ ጎንደር እናአዲስ አበባ የትራንስፖርት አገልግሎት፣ የማረፊያ እና መስተንግዶ እንደሚገኙበትም ጠቁሟል። 200 ለሚጠጉ ኬንያውያን፣ 200 ለሚሆኑ ኡጋንዳውያን እና 800 ለሚሆኑ ሶማሊያውያን በቂ እገዛ ማድረጉን በአብነት አስቀምጧል።

በሱዳን የተፈጠረውን ቀውስ ተከትሎ በመተማ በኩል የገቡ ስደተኞች ውስጥ 39 በመቶ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን፣ 17 በመቶ ሱዳናውያን እና 13 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ቱርካውያን መሆናቸውን ያስታወቀው ድርጅቱ ከነዚህ ውስጥም ሃያ በመቶ የሚሆኑት ህጻናት ናቸው ብሏል።

በሌላ ዜና የሱዳን ተቀናቃኝ ሀይሎች በሳዑዲ አረብያ ተገናኝተው እንደሚመክሩ ኒውዮርክ ታይምስ በድረገጹ አስነብቧል። የሁለቱም ጀነራሎች ተወካዮቻቸው በሳዑዲ ተገናኝተው ዘላቂ የሰላም ስምምነት ይፈራረማሉ ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ የአሜሪካ ባለስልጣናት እንደገለጹለት ድረገጹ አስነብቧል።

ውይይቱን ያዘጋጁት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤት እና የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሆናቸውን ዘገባው ጠቁሟል። የሱዳን ወታደራዊ ሀይል ተወካዮች ትላንት ማታ ወደ ሳዑዲ ማቅናታቸውን የጦር ሃይሉ በይፋዊ የማህበራዊ ሚዲያ ፌስቡክ ገጹ ማስታወቁን ዘገባው አካቷል። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.