ዜና፡ በአዲስ አበባ በሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ረዥም ሰልፍ እየተስተዋለ በመሆኑ ቅሬታ ቢቀርብም ምንግስት የክፍያ ስርዓቱ ዲጂታል እንደሚቀጥል አረጋገጠ

በሞላ ምትኩ @MollaAyenew

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 21/ 2015 ዓ.ም፡- የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክ ሚኒስቴር በመዲናዋ ውስጥ ባሉ በርካታ የነዳጅ ማደያዎች ላይ የሚስተዋለው ረጅም ሰልፍ የትራፊክ መጨናነቅ እና መስተጓጎል እያስከተለ ባለበት ሁኔታ የነዳጅ ግብይት ሙሉ በሙሉ በዲጂታል እንዲከናወን በወሰነው ውሳኔ እንደሚቀጥል አስታወቀ።

ተግባራዊ መሆን የጀመረው ዲጂታል  ክፍያን ተከትሎ  አሽከርካሪዎች ነዳጅ ለመሙላት ለሰዓታት እየጠበቁ መሆኑን ቅሬታ አቅራቢዎች ይገልፃሉ። አዲስ ስታንዳርድን ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎች በአብዛኛው ድርጊቱን የሚደግፉ ቢሆንም በነዳጅ ማደያዎች አካባቢ ያለው ረጅም ወረፋ እና መስተጓጎል የስራ ሰዓታቸውን እየተሻማባቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡

አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ ያልፈለጉ አሽከርካሪ እንዳሉት ዲጂታል የማድረጉ ስራ ቀስ በቀስ መተግበር የነበረበት ሲሆን አሁን ያለውን ችግር ለማስወገድ አሽከርካሪዎች ዲጂታል የክፍያ ዘዴዎችን እስኪያጠናቅቁ ድረስ ሁለቱንም አማራጮች እንዲጠቀሙ ሊደረግ ይገባል ብለዋል።

የነዳጅ ግብይቶችን ዲጂታል ማድረግ የተጀመረው በሚኒስትሮች ምክር ቤት ታህሳስ 2022 ባስተላለፈው  ውሳኔ  መሰረት መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር ገልጧል፡፡

በሚኒስቴሩ የነዳጅ ድጎማ ፕሮጀክት አስተባባሪ ሰልማን መሀመድ ለአዲስ ስታንዳርድ እንደተናገሩት “ከሀምሌ 2022 ጀምሮ የመንግስት የነዳጅ ድጎማ ፕሮግራም ተጠቃሚ በሆኑ ከ200 ሺህ በላይ የትራንስፖርት ተሽከርካሪዎች ላይ የዲጂታል ክፍያ ተፈፃሚ ሆኗል” ብለዋል። በ200 ሺህ ተሸከርካሪዎች ላይ ከዘጠኝ ወራት ትግበራ ከተደረገ በኋላ በአዲስ አበባ ወደ ሙሉ የዲጂታል የክፍያ ስርዓት መገባቱን  ሰልማን ተናግረዋል፡፡

በነዳጅ ማደያዎቹ የሚስተዋለው ረጅም ሰልፍ የተከሰተው በዋናነት ተጠቃሚዎቹ በሙከራ ጊዜ ውስጥ ዲጂታል ለማድረግ የሚያስፈልጉ ቅድመ ዝግጅቶችን ባለማጠናቀቃቸው ነው ብለዋል። በተጨማሪም በአንዳንድ ነዳጅ ማደያዎች ያለው የሰራተኞች እጥረት ለረዘመ ወረፋ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል።

ረዣዥም ወረፋ ባለባቸው አንዳንድ የነዳጅ ማደያዎች አፋጣኝ ውሳኔዎች እየተላለፉ መሆኑን የገለፁት አስተባባሪው መንግሥት ውሳኔውን ለመቀልበስ እንዲሁም እንደ አማራጭ የጥሬ ገንዘብ ክፍያን ስራ ላይ እንዲውል ለማድረግ ምንም ፍላጎት እንደሌለው አስረድተዋል።

አቶ የኋላእሸት ታምሩ የኮርፖሬት ቢዝነስ ጠበቃ  ሲሆኑ ውሳኔው በብር መግዛትን እና መሸጥን የሚገድብ ሳይሆን የክፍያ ስርዓቱን ወደ ዲጂታል የሚቀይር አሰራር ነው ሲሉ ለአዲስ ስታንዳርድ አስረድተዋል፡፡

እንደ ጠበቃው ከሆነ መንግስት የጥሬ ገንዘብ ክፍያን መከልከሉ በገበያው ውስጥ ያለው የገንዘብ እጥረት እና በነዳጅ ግዥ ላይ የሚታዩ የረዥም ጊዜ ሕገ-ወጥ ድርጊቶችን ለመከላከል ይረዳል ብለዋል፡፡ አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.