ዜና፡- በነሐሴ ወር ወታደራዊ ግጭት ካገረሸበት ጊዜ ጀምሮ በትግራይ፣ አፋር እና አማራ ክልሎች ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ሰዎች ተፈናቅለዋል፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት

ተፈናቃዮች በትግራይ ክልል

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 21/ 2015 ዓ.ም፡- በሰሜን ኢትዮጵያ በነሐሴ ወር መጨረሻ ጦርነት ካገረሸበት ጊዜ አንስቶ በአፋር፣ አማራ እና ትግራይ ክልሎች በተከሰቱ ግጭቶች ወደ 574,000 የሚጠጉ ሰዎች ተፈናቅለዋል ሲል ዩኒሴፍ አዲስ ያወጣው ሪፖርት ያመለክታል፡፡

የዩኒሴፍ ሪፖርት እንደሚያመለክተው በመላው ኢትዮጵያ የሰብዓዊ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ቁጥር 29.7 ሚሊዮን ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 12.5 ሚሊዮን ያህሉ ህፃናት ናቸው፡፡

ከፍተኛ ጉዳት በደረሰበት የትግራይ ክልል በነሀሴ ወር መጨረሻ ላይ ጦርነት ካገረሸበት ጊዜ አንስቶ “በተከታታይ የአየር ጥቃት እና በተለያዩ ግንባሮች ድብደባ የተነሳ ከ210,000 በላይ ሰዎች ተፈናቅለዋል” ሲል ሪፖርቱ አክሎ ገልጿል፡፡

ሪፖርቱ በአፋር ክልል ግጭት በተከሰተባቸው የትግራይ አዋሳኝ ዞኖች ውስጥ እሰከ መስከረም 30/ 2015 ዓ.ም  ድረስ ተጨማሪ 163,709 ሰዎች ተፈናቅለዋል፣ በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ እና ዋግ ህምራ ዞኖች ደግሞ ከ200,000 በላይ ሰዎች አዲስ የተፈናቀሉ መሆናቸውንም አክሎ ገልጿል፡፡

ቅዳሜ ጥቅምት 29፣ 2015 ዓ.ም የወጣው ሪፖርት “በደህንነት ስጋት እና በእርዳታ እንቅስቃሴዎች ላይ የሚደረጉ ገደቦች በሶስቱ ክልሎች የሰብኣዊ እርዳታ ምላሽን መገደባቸውን ቀጥለዋል” ብሏል፡፡

በትግራይ “ከሐምሌ እስከ መስከረም ወር ባለው ጊዜ ውስጥ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና አገልግሎት የሚያገኙ ህጻናት፣ ነፍሰ ጡር እና የሚያጠቡ ሴቶች ቁጥር 84 በመቶ ገደማ ቀንሷል” ሲል ሪፖርቱ ገልጧል።

በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ፣ ሰሜንና ምዕራብ ጎንደር እና በዋግ ኽምራ ዞኖች 625 ትምህርት ቤቶች ዳግም በተቀሰቀሰው ግጭት ምክንያት የተዘጉ ሲሆን ከ500,000 በላይ ህጻናት ከትምህርት ገበታ መፈናቀላቸውን ዩኒሴፍ ገልጧል።

ድርጅቱ ችግር ቢገጥመውም በትግራይ፣ አፋር እና አማራ ላሉ 23,062 ህጻናትና ሴቶች የመጀመሪያ ደረጃ የጤና አገልግሎት ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል።

ዩኒሴፍ  የወጣው ዘገባ ጦርነቱ በአስቸኳይ እንዲቆም እና እያንዣበበ ያለውን ቀውሱን ለማስቀረት እጅግ አስፈላጊ የሆነውን ሰብዓዊ ርዳታ ዳግም እንዲጀመር ዓለም አቀፉ መህበረሰብ ጥሪዎች እየተበራከቱ  በመጡበት ወቅት ነው።

የኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች እና የትግራይ ክልል ልዑካን በደቡብ አፍሪካ ከጥቅምት 15 ቀን ጀምሮ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚያስችል መፍትሄ ለማፈላለግ ወደ ደቡብ አፍሪካ ማምራታቸው ይታወቃል፡፡ አፍሪካ ህብረት መራሹ የሰላም ድርድር ትላንት እሁድ ጥቅምት 20 ይጠናቀቃል ተብሎ ነበር። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.