ዜና፡ በበርካታ የኦሮምያ ክልል አከባቢዎች በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት እና በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች መካከል ከፍተኛ ውጊያ በመጋሄድ ላይ መሆኑ ተገለጸ፣ በርካታ ንጹሃን ተገድለዋል

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 10/2015 ዓ.ም፡- በከባድ መሳሪያ የታገዘ ከፍተኛ ውጊያ በበርካታ የኦሮምያ ክልል አከባቢዎች በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት እና በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች መካከል በመጋሄድ ላይ መሆኑ ነዋሪዎቸ ለአዲስ ስታንዳርድ አስታወቁ። በውጊያው በርካታ ንጹሃን መገደላቸውንም ገልጸዋል። በኦሮምያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በአምቦ ወረዳ የዋዴሳ በምትባል ቦታ ነዋሪ የሆኑ እና ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ ለአዲስ ስታንዳርድ እንዳስታወቁት በአከባቢው ከግንቦት 7 እስከ 9 ቀን 2015 ዓ.ም በተካሄደ ውጊያ አምስት ንጹሃን ገበሬዎች  ተገድለዋል።

“እኔ የማውቃቸው በትንሹ አምስት የሚሆኑ ገበሬዎች በውጊያው ተገድለዋል። ከባድ መሳሪያዎች ይተኮስ ነበር፤ አንዳንድ የተተኮሰው ከባድ መሳሪያ በመኖሪያ አከባቢ በማረፉ ምክንያት ገበሬዎቹ እና ከብቶቻቸው ሞተዋል” ሲሉ ነዋሪው ገልጸዋል።

በተፋላሚዎቹ መካከል ከባድ ጉዳት ማስተናገዳቸው የማይቀር መሆኑን ነዋሪው ከነበረው ከባድ ውጊያ እና ይሰማ የነበረው የከባድ መሳሪያ ድምጽ የተነሳ ያላቸውን ፍራቻ ጠቁመዋል፤ በሂወቴ የዚህ አይነት ውጊያ ሰምቼ አላውቅም ሲሉ ሁኔታውን ገልጸዋል።

የሰላም ድርድር እየተካሄደ መሆኑን ስንሰማ ጦርነቱ ያቆማል የሚል ተስፋ እንድንሰንቅ አድርጎን ነበር ያሉት ነዋሪው ሁኔታው መሻሻል ከማሳየት ይልቅ እየባሰበት መጥቷል ሲሉ ለአዲስ ስታንዳርድ አስታውቀዋል።

በሆሮዱሩ ዞን የኮምቦልቻ ነዋሪ የሆኑ እና ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ ግለሰብ በበኩላቸው በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት እና በመንግስት ሀይሎች መካከል ግንቦት 9 ቀን 2015 ዓ.ም ቀትር ላይ ከፍተኛ ውጊያ እንደነበር ለአዲስ ስታንዳርድር ገልጸዋል። ከፍተኛ ውጊያ ከተደረገ በኋላ የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት አባላት ከተማዋን መቆጣጠራቸውን እና የፖለቲካ እስረኞችን መፍታታቸውን ነዋሪው አስታውቀዋል። “የምርጥ ዘር ማከማቻ የነበረን መጋዘን በመስበር በውስጡ የነበረውን ምርጥ ዘር በከተማዋ ለሚገኙ ገበሬዎች አከፋፍለዋል፤” ብለዋል ነዋሪው። አክለውም በውጊያው ሳቢያ በርካታ የከተማዋ ቤቶች መቃጠላቸውን ተናግረዋል። ከተማዋን ከመቆጣጠራቸው በፊት ከከተማዋ በ24 ኪሎሜትር ርቀት የምትገኝ ዳዱ የተባለች ትንሽ ከተማ ላይ በሁለቱ ሀይሎች መካከል ከፍተኛ ውጊያ ሲካሄድ እንደነበርም ገልጸዋል።

በሆሮጉዱሩ ዞን በሱሉላ ፊንጫ ወረዳ የፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ሰራተኛ የሆኑ ነዋሪ እና ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸው እንዲጠቀስ ያለፈለጉ በበኩላቸው በፊንጫ ስኳር ፋብሪካ አቅራቢያ ለሁለት ቀናት የዘለቀ ከፍተኛ ውጊያ እንደነበር እና አንዳንድ የአከባቢው መንደሮችም በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት እንደሚተዳደሩ ገልጸዋል።

በቅርቡ በኦሮምያ በርካታ አከባቢዎች እየተካሄደ ስላለው ውጊያ በመንግስት በኩል የተባለ ነገር የለም። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.