ዜና፡ሶስት የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች የጃዋር መሀመድን የጥበቃ አባላት ዋስትና ከፈቀዱ በኋላ መታሰራቸው ቅሬታ አስነሳ

አዲስ አባባ፣ጥቅምት26/2015 ዓ.ም፡- በኦሮሚያ ክልል የምስራቅ ሸዋ ዞን አዳማ ከተማ ፖሊስ፣ በኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የምስራቅ ወንጀል ችሎት ሶስት ዳኞችን ያለህግ አግባብ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ እና ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የመረጃ ምንጭ ለአዲስ ስታንዳርድ ተናግረዋል፡፡

ደሳለኝ ለሚ፣ መሀመድ ጂማ እና አብዲሳ ዋቅጅራ የተባሉ ሶስት የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች አርብ ጥቅምት 25፣ 2015 ዓ.ም ከቀኑ 8፡40 ስዓት ኣካባቢ በፍርድ ቤቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ በሚገኘው ቢሯቸው እያሉ በአዳማ ከተማ ፖሊስ አባላት ተይዘው መወሰዳቸውን የመረጃ ምንጩ ለአዲስ ስታንዳርድ ገልፀዋል፡፡

ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ የመረጃ ምንጫችን ፖሊስ ዳኞቹን ከሽብርተኝነት ጋር በተያያዙ ወንጀሎች ጠርጥሮ መያዙንyeT ገልፀዋል፡፡ ሆኖም እስራቸው የመጣው የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት የአቶ ጃዋር መሀመድ ስድስት የጥበቃ አባላት በዋስ እንዲለቀቁ ከወሰኑ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ነው፡፡ የጥበቃ አባላቱ በያዝነው አመት ጥቅምት ወር የኢሬቻ በዓል አከባበር ወቅት በድጋሚ የታሰሩ ሲሆን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡

የዳኞቹ መታሰር በማህበራዊ ሚዲያው በህግ ባለሙያዎች ዘንድ ቅሬታን የቀሰቀሰ ሲሆን የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት መዓዛ አሸናፊ እና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለም አዉግዘዉታል፡፡

መአዛ “እስሩ እጅግ አሳሳቢ ነው” ሲሉ አውግዘው “የዳኞችን ያለመከሰስ መብት ለማንሳት እና ወንጀል ፈጽመዋል ተብለው ሲጠረጠሩ በቁጥጥር ስር ለማዋል ሊከተሉት የሚገባ ጥብቅ አሰራር አለ” ብለዋል። አክለውም “ይህ ድርጊት የዳኞችን እና የተቋማቸውን ነፃነት በእጅጉ የሚጎዳ በመሆኑ ሁኔታዉን በማጣራት ዉሳኔዉ እንዲቀለበስ እየሞከርን ነው “ ሲሉ ገልፀዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) በበኩላቸው “እስራቱ ፈጽሞ ሕገወጥና በዳኝነት ነጻነት ላይ የተፈጸመ ጥቃት ነው” ብለዋል።

እንደ ኢሰመኮ ገለፃ ዳኞቹ የታሰሩት ከወረዳ ፍርድ ቤት በተሰጠ ትዕዛዝ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ታሳሪዎቹ ዳኞች መሆናቸውን እንደተረዳ የእስር ትእዛዙን የሻረ መሆኑን አሳውቋል፡፡

ሆኖም ይህ ዜና እስከተወጣበት ጊዜ ድረስ ዳኞቹ በአዳማ ከተማ ዳምባላ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው መቆየታቸውን አዲስ ስታንዳርድ አረጋግጣለች።

የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በዳኞቹ መታሰር ላይ መግለጫ አልሰጠም። አዲስ ስታንዳርድ ከፍርድ ቤቱ መረጃ ለማግኘት ያደረገችው ሙከራ አልተሳካም። አስ

No comments

Sorry, the comment form is closed at this time.